የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኮሮና ቫይረስን ለመከላከል የሚደረጉ ጥረቶችን ለማገዝ የአሥር ሚሊዮን ብር ድጋፍ ከመሰጠቱም ባሻገር፣ ወደፊትም ለዚሁ ተግባር ድጋፍ እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡
መጋቢት 10 ቀን 2012 ዓ.ም. በባንኩ ዋና መሥሪያ ቤት የገንዘብ ድጋፉን አስመልክቶ የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ እንደገለጹት፣ ወረርሽኙን ለመከላከል ለተዘጋጁ ለይቶ ማቆያ ማዕከሎች ውስጥ የተጓደሉ የሕክምና መሣሪያዎችን ለማሟላት፣ ለንጽሕና መጠበቂያ ሳሙናዎች፣ ለእጅ ጓንቶች፣ ለፊት መሸፈኛ ጭንብሎች፣ ለሳኒታይዘሮችና ለሌሎች ቁሳቁሶች ማሟያ የሚውል ነው፡፡
እንዲህ ዓይነቱ ድጋፍ የወረርሽኙ ሥርጭት ጊዜ የማይሰጥ በመሆኑ መጠናከር እንዳለበት የጠቀሱት አቶ አቤ፣ በባንካቸው በኩል አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል፡፡
ከዚህ ባሻገር ባንኩ በ1,560 ቅርንጫፎቹ ለሚስተናገዱ ደንበኞች አስፈላጊዎቹን የጽዳት ዕቃዎች በማቅረብ እንዲስተናገዱ ማድረግ እንደጀመረ ገልጿል፡፡
ባንኩ ያበረከተውን አሥር ሚሊዮን ብር የጤና ሚኒስትር ዴኤታዋ ወ/ሮ ሳህሬላ አብዲላሒ ተረክበዋል፡፡