የፌዴራል መንግሥት ሠራተኞች ከቤት ሆነው እንዲሠሩ ተወሰነ
ኢትዮጵያ ቻይናዊው የአሊባባ ባለቤት ጃክ ማ ለአፍሪካ አገሮች ከለገሱት የኮሮና ቫይረስ መመርመርያ መሣሪያዎች (ኪቶች) በተጨማሪ፣ 52 ሺሕ መመርመሪያ ኪቶችን ከሌሎች የቻይና አጋሮቿ አገኘች።
በአዲስ አበባ የሚገኘው የቻይና ኤምባሲ በትዊተር ገጹ እንዳስታወቀው መቀመጫውን በአዲስ አበባ ያደረገው የቻይና አፍሪካ የንግድ ምክር ቤት፣ 22 ሺሕ የመመርመሪያ ኪቶችንና ተንቀሳቃሽ የቫይረሱ መመርመሪያ መሣሪያዎችን ለኢትዮጵያ ለግሷል።
በተጨማሪም ቢጄአይ የተባለ ተቋምና ማሞዝ የተባለ ፋውንዴሽን በጋራ በመሆን፣ 30 ሺሕ የመመርመሪያ ኪቶችን ለኢትዮጵያ ማበርከታቸውን ኤምባሲው አስታውቋል።
አሊባባ የተባለው የቻይና ኩባንያ ባለቤት ለሁሉም የአፍሪካ አገሮች 1.1 ሚሊዮን መመርመሪያ ኪቶችን በቅርቡ መለገሱ የሚታወቅ ሲሆን፣ ይህም ለሁሉም የአፍሪካ አገሮች በዕኩል 20 ሺሕ ኪቶች የኢትዮጵያ መንግሥት ባቀረበው የሎጂስቲክስ ድጋፍ በመከፋፈል ላይ ነው።
ኢትዮጵያም ከዚህ ድጋፍ ውስጥ 20 ሺሕ ኪቶች የሚደርሷት በመሆኑ፣ ከቻይና አጋሮቿ ያገኘቸውን የመመርመሪያ ኪቶች አጠቃላይ የመመርመሪያ ኪቶቿ ድጋፍ ከ72 ሺሕ በላይ ያደርሰዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የሚኒስትሮች ምክር ቤት የኮሮና ቫይረስ ሥርጭትን ለመከላከል ከመጋቢት 16 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ የፌዴራል የመንግሥት ሠራተኞች ሥራቸውን በቤታቸው ሆነው እንዲያከናውኑ ወስኗል።
የጠቅላይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ጽሕፈት ቤት ባወጣው መግለጫ እንደገለጸው ተጨማሪ ውሳኔ እስከሚተላለፍ ድረስ የፌዴራል መንግሥት ሠራተኞች ሥራቸውን ከቤታቸው ሆነው ይቀጥላሉ፡፡ ከቤታቸው ሆነው የሚሠሩ የመንግሥት ሠራተኞች በእያንዳንዱ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤት አማካኝነት በሚወጣ ደንብ የሚለዩ ሲሆን፣ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶቹ ለሠራተኞቻቸው ማን ከቤት ሆኖ እንደሚሠራ እንደሚያስታውቁ ገልጿል። ይህ ውሳኔ የተወሰነው በመላው አዲስ አበባ የሚካሄድ እንቅስቃሴንና የትራንስፖርት ዘርፉን መጨናነቅ ለመቀነስ ታስቦ መሆኑንም አስታውቋል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ከ289 ሠራተኞችና አማካሪዎች መካከል 184 ለሁለት ሳምንታት ሥራቸውን ከቤታቸው ሆነው እንዲያከናውኑ ተወስኗል፡፡ ይህም ከጠቅላላው የሰው ኃይል 64 በመቶ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የፕላንና ልማት ኮሚሽንም በሥሩ ከሚገኙ ተጠሪ መሥሪያ ቤቶች ጋር በመሆን፣ ከአጠቃላይ ሠራተኞች 80 በመቶ የሚሆኑት ከቤታቸው ሆነው እንዲሠሩ መወሰኑን አስታውቋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥር ባሉ ተቋማት ከወሳኝ የሥራ ሒደት ውጪ ያሉ ሠራተኞችም፣ በተመሳሳይ ከቤታቸው ሆነው ላላተወነ ጊዜ እንዲሠሩ አስተዳደሩ መወሰኑን የገለጸ ሲሆን፣ ይህም ከመጋቢት 16 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚሆን ተገልጿል።