የቶኪዮ 2020 ኦሊምፒክ ዝግጅት ከመጀመሩ አስቀድሞ በከፍተኛ አለመግባባት ውስጥ ሆነው የዘለቁት የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ችግሮቻቸውን እንዲፈቱ ስፖርት ኮሚሽን አሳስቧል፡፡ ከሰሞኑ ከቶኪዮ ኦሊምፒክ ዝግጅት ጋር ተያይዞ አለመግባባቱ አፍጥጦ መውጣቱ ብዙዎችን አነጋግሯል፡፡
አሁን ላይ የዓለም መንግሥታትን ክፉኛ እየተፈታተነ የሚገኘው ኮሮና ቫይረስ (ኮቪዲ 19) ጥላውን ካጠላባቸው መካከል ቶኪዮ 2020 ኦሊምፒክ ዋነኛው ነው፡፡ ቀደም ሲል የዓለም አቀፍ ኦሊምፒክ ኮሚቴ (አይኦሲ) እና አዘጋጇ ጃፓን ቶኪዮ ኦሊምፒክ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መሠረት እንደሚከናወን መናገራቸውን ተከትሎ ኢትዮጵያን ጨምሮ ተሳታፊ አገሮች ሥጋት ውስጥ መግባታቸው አልቀረም፡፡
ለቶኪዮ ኦሊምፒክ በብሔራዊ ደረጃ የዝግጅትና የቴክኒክ ኮሚቴዎችን አዋቅሮ ሲንቀሳቀስ የቆየው የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ፣ ከሰሞኑ ብሔራዊ አትሌቶች በሆቴል ተሰባስበው ዝግጅት እንዲጀምሩ ማለቱን ተከትሎ፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ውሳኔውን በመቃወም ቀዝቀዝ ብሎ የነበረውን የሁለቱን ተቋማት አለመግባባት እንደ ገና እንዲያገረሽ አድርጎታል፡፡
ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን ጨምሮ በመንግሥት የተደነገገውን ክልከላ ተከትሎ ‹‹አትሌቶች በሆቴል መሰባሰብ የለባቸውም›› የሚለው የፌዴሬሽኑ ተቃውሞ በኅብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ መንግሥት በጉዳዩ ጣልቃ ሳይገባ ሆኖም ስፖርት ኮሚሽን ሰኞ መጋቢት 14 ቀን 2012 ዓ.ም. የሁለቱን ተቋማት አመራሮች በቢሮው ጠርቶ ለውዝግብ በዳረጋቸው ጉዳይ ተነጋግረው ውሳኔቸውን እንዲያሳውቁ ግዴታ ውስጥ መግባታቸው ታውቋል፡፡
ይህ ዘገባ እስከ ተጠናቀረበት ድረስ ሁለቱ ተቋማት ስለደረሱበት ነጥብ የታወቀ ነገር ባይኖርም፣ በቶኪዮ ኦሊምፒክ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ላይ ከተጋረጠው አደጋ በመነሳት የጋራ አቋም እንደሚይዙ ይጠበቃል፡፡