ዘመኑ የፍርኃት፣ የኮሮና በሽታ ሥጋት ላይ ነን ያለነውና እንጠንቀቅ፡፡ መከላከያ ናቸው የተባሉትን ነገሮች እንተግብራቸው፡፡ አገሬ ኢትዮጵያ ግን ከፖለቲካ አክቲቪስቶች፣ ከፖለቲካ ነጋዴዎች በፊት ነበረች፡፡ በኮሮና ዘመንና በኋላም ትኖራለች፡፡ እስኪ በየትኛውም ደግና ክፉ ዘመን የማይነኩ ነገሮች ይኑሩን፡፡
ለእኔ ከማይነኩ ነገሮች መካካል አንዱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው፡፡ እኔ ከበደ፣ አንተ ሞቱማ፣ ወይም ዋቅጂራ፣ ወይም ገብረ ፃዲቅ ወይም ሌላ…. ዓለም አያውቀንም፡፡ የእኔና የአንተ ቀለም የሆነው፣ የእኛ አውሮፕላን ግን የኔና የአንተን ግፍና ተንኮል ተሸከሞ ዓለም ያውቀን ዘንድ ሲበር ይኖራል፡፡ አንንካው [አንንካው ማለት አንሞግተው ማለት አይደለም]፡፡
ግን ደግሞ ስም ማጥፋት ሌላ፣ መሞገት ደግሞ ሌላ ነው፡፡ አይደለም ዛሬ ትናንት የአገሬ ብቻ ጌጥ ሳይሆን የአፍሪካ ኩራት ሆኖ ሲበር እንደኖረ ለመገንዘብ የኔልሰን ማንዴላን “Long Walk to Freedom“ የተሰኘውን ግለ ታሪክ መጽሐፍ ማንበብ በቂ ነው፡፡ እናስ? የእኔ፣ የአንተ፣ የእኛ መለያ ቀለም የሆነውን አየር መንገድ ስትነካው እኔን ያመኛል፡፡
ስለዚህ እሞግትሃለሁ! ከምንም በለይ በእኛ በዜጎቹ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስሙ ሲጠፋ ከመስማት በላይ፣ በሽታና ሕመም የለምና እሞግትሃለሁ! ስም ማጥፋቱ ከኬንያ ዜጋ፣ ከዱባይ ˝አቪዬሽን˝ ባለሙያ፣ ከሉፍታንዛ አውሮፕላን ሠራተኞች ቢሆን አያመኝም፡፡ ከእኛው ሲሆን ግን እጅግ በጣም ያሸማቅቃልና ታጥቄ እሞግትሃለሁ!
በልበ ሙሉነት መናገር እችላለሁ፡፡ በዓለም የሰዓት መመዘኛ መሠረት በአገሬ ሥራን ሠርተው ከሚኖሩ ድርጅቶች ውስጥ አንድ ጥራ ብትባል ቀዳሚው የአገሬን፣ የኢትዮጵያን አየር መንገድ እንደምትጠራ አልጠራጠርም፡፡ ታዲያ ይህ ግዙፍ የእኛ ዓርማ፣ በእኛው በአገሬው ዜጎች ስሙ ሲጠፋ ያሳዝናል፣ ያበግናልም፡፡
ከዚህ በላይ የሚያም፣ ከዚህ በላይ በእኔና በአንተ እንደ ዜጋ የተቃጣ ጥቃትም አይኖርም፡፡ ወደፊትም አይፈጠርም፡፡ ሊከፈለው ነው የጻፈው ወይም የኢትዮዽያ አየር መንገድ ቃለ አቀባይ ነው ብለህ ልታማ ትችላለህ፡፡ በምን ዕድሌ የእኔ ወንድም!
በሕይወት እያለሁ ግን አየር መንገዴ ቀለሜ ነውና ሳይከፈለኝ ቃል አቀባዩ ነኝ ስልህ በኩራት ነው፡፡ ዓለም አቀፍ የ‹‹አቪዬሽን›› ኢንዱስትሪ ውድድር እኔና አንተ እንደምናስበው ጉሊት ድንች ገዝቶ ቀቅሎ እንደ መብላት ቀላል አይደለምና ጉዳዩን ለሚመለከተው እንተወው፡፡ አየር መንገዴን ማማት፣ ስሙን ማጥፋት ግን በእኛ በዜጎቹ አያምርም!
የእኔ ወንድም ወዳጀ እንዲያው ስሞትልህ ድርጅቱ ቢያጠፋ እንኳን፣ በእኔና በአንተ ስሙን ማንቋሸሽ ተገቢ አይደለምና አትንካው! አትንካው ስልህም ደግሞ አትንካው ነው!! ስትነካው ያመኛል! ብዙዎቻችንን ያመናል! እናም እባክህን አ–ት–ን–ካ–ው!!!
እንደ አገር የማይነኩ ግለሰቦችም ደግሞ ያስፈልጉናል፡፡ ለእኔ ለምሳሌ ኃይሌ ገብረሥላሴ ቢያጠፋ እንኳን ‹‹ኃይሌን ምን ነካው?›› ተብሎ ይታዘንለታል እንጂ ኃይሌ አይነካም፡፡ ኃይሌ አይሰደብም፡፡ ኃይሌ ቀለሜ፣ ኃይሌ ቀለማችን ነው፡፡
እንደምናውቀው እኔን ተራውን አንተን ብዙ ተከታይ ያለህን የፖለቲካ ተንታኝ ዓለም አያውቀንም፡፡ የኃይሌ ስም ሲጠራ ግን ስለኢትዮዽያ ብቻ ሳይሆን ስለጥቁር አልሸነፍ ባይነት ሲባል ዓለም አንተን፣ እኔን፣ መላውን ጥቁር የአፍሪካ ዜጋ በሙሉ ያውቀናል፡፡ ምናልባት በዕርዳታ የበላነው ስንዴና ዘይት፣ በብድር፣ በደመወዝ ስም ኪሳችን የገባው የውጭ የዕርዳታ ገንዘብ ‹‹የኃይሌ አገር ሰዎች እየተቸገሩ ስለሆነ እንርዳቸው›› ተብሎ የመጣ ይሆናል፡፡
ማን ያውቃል?! ከምንም ከማንም በላይ ደግሞ በባንዲራችን ፊት ስለወረደ ዕንባው፣ ስለአገሩ ሲል እግሩ ላይ ስለፈሰሰው ደሙ ሲባል ኃይሌ አይነካም፡፡ እደግመዋለሁ በሌላው ዓለም እንደ ኃይሌ ዓይነቱ ብርቱ ዜጋ ቢያጠፋ እንኳ ይታዘንለታል እንጂ፣ በገዛ የአገሩ ዜጎች አፍ አይከፍትበትም፡፡ ምክንያቱም አገር ቢያጠፉ እንኳ የማትነካቸው ዜጎች ያስፈልጓታልና ነው፡፡
በመጨረሻ ግን ደግሞ በቀዳሚነት አገር አትነካም! በስድሰት ወራት የአሜሪካ ቆይታህ ምን ተምረህ መጣህ ብትለኝ ትምህርት ከመቅሰም ባሻገር፣ የቱን ያህል ልዩና የተለየ ሐሳብ ቢኖራቸው አሜሪካኖች አገራቸውን አይነኩም፡፡ ፖለቲካ ሌ፣ መደገፍ ሌላ፣ መቃወም ሌላ፣ ጉብዝና ሌላ፣ ስንፍና ሌላ፣ ብሔር፣ ጎሳ፣ መስፋት መጥበብ ሌላ! በዚህ ውስጥ ግን አሪፍና ትምህርት የገባህ ከሆንክ አገርህን አትነካም፡፡
የእኔን ጠቅላይ ሚኒስትር መቃወም፣ መደገፍ፣ አቅም ካለህ በሐሳብ መሞገት ትችላለህ፡፡ አገሬን መንካት ግን አትችልም፡፡ ሕወሓት መሆን መብትህ ነው፡፡ ኦፌኮ መሆን መብትህ ነው፡፡ ብልፅግና ሁን አሁንም መብትህ ነው፡፡ ከፈለግህ በምርጫ ቦርድ ተመዝግበህ ብቻህን ፓርቲ ሁን ግድ የለኝም፡፡ የፈለግከውን ሆነህ ግን የማይነካ ነገር ሊኖርህ ያስፈልጋል፡፡
አንዷና ዋነኛዋ እናት አገርህ ናት፡፡ ያውም እንደፈለግን የምንኖርባት እናት አገራችን ኢትዮጵያችን አትነካም፡፡ እሷ በየትኛውም መሥፈርት ከማይነኩ ነገሮች ዋነኛዋና ቀዳሚዋ ናት! እንደ አገር ለእኛ አልፋና ኦሜጋችን ናት፡፡
እናትህን እንደማትነካት ሁሉ እሷንም አትንካት!
እ–ን–ዳ–ት–ነ–ካ–ት!!!
ከኮሮና ይጠብቀን ዘንድ እንጠንቀቅ!
ፈጣሪም የመጣውን ያቅልልን!!
(ተስፋዬ እሸቱ፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ)