የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቤቶች ልማት አስተዳደር ቢሮና በሥሩ የሚገኙ ሦስት ተቋማት 1,185 ሠራተኞችን ከሥራ ማገዳቸው ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ፡፡
ቢሮው፣ የቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን፣ የቤቶች ዲዛይን ጽሕፈት ቤትና የቤቶች ግንባታ ኢንተርፕራይዝ ከሁለት እስከ 15 ዓመታት ይሠሩ የነበሩ ቁጥራቸው የተጠቀሰውን ሠራተኞች፣ አዲስ የሥራ ምደባ መዋቅር ውስጥ ከሚያዝያ 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ እንዳልተካተቱ ወይም እንዳልተመደቡ የሚገልጽ ዝርዝር፣ በየተቋማቱ ሰሌዳ ላይ ተለጥፎ መመልከታቸውን ሪፖርተር ያነጋገራቸው ሠራተኞች ተናግረዋል፡፡
ቁጥራቸው መብዛቱን ሲመለከቱ የት እንደተመደቡ ለማወቅ ወደ ሰሌዳው ቀርበው ሲመለከቱ፣ ‹‹ያልተመደቡ ሠራተኞች›› የሚል አባሪ ደብዳቤ ማንበባቸውን አስረድተዋል፡፡ ስማቸውን እስከ መጠራጠር ደርሰው ‹‹የተለጠፈው ስም ዝርዝር ትክክል ነው?›› በማለት እርስ በርሳቸው መጠያየቃቸውን የሚናገሩት ሠራተኞቹ፣ ምክንያታቸው ደግሞ አገር በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ጭንቅ ውስጥ ባለችበት በዚህ ጊዜ ይህንን ሰብዓዊነት የጎደለው ድርጊት ይፈጸማል የሚል እምነት ስለሌላቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በአራቱም ተቋማት ሥር ያሉትን ሠራተኞች በአዲስ መዋቅር በማደራጀት፣ በሙያቸውና በችሎታቸው ለመመደብ የተለያየ ቁጥር ያላቸው ሁለት ኮሚቴዎች ተቋቁመው ለዓመታት ሲሠራ መቆየቱን ሠራተኞቹ ተናግረዋል፡፡ ኮሜቴዎቹ በወጣው መሥፈርት መሠረት ከሁለት ዓመታት እስከ 15 ዓመታት ሲሠሩ የነበሩ ቋሚ ሠራተኞችን እንደ ችሎታቸውና ብቃታቸው ይመድባሉ ተብሎ ሲጠበቅ የነበረ ቢሆንም፣ ወረርሽኙ ጭንቀት በፈጠረበት ወቅት ከተመደቡት የሚበልጥ ሠራተኞችን ከሥራ ውጪ ማድረግ ምን ማለት እንደሆነም እንዳልገባቸው አስረድተዋል፡፡
የጤና ባለሙያዎችና መንግሥት በአስቸኳይ አዋጅ ጭምር በመታገዝ ሕዝቡን እያስጠነቀቁ ባሉበት በዚህ ወቅት ያልተገመተና ድንገተኛ ማስታወቂያ በተቋማቱ በመለጠፉ፣ ሠራተኞች ‹‹ተራራቁ›› የሚለውን ረስተው ያልተመደቡበትን ምክንያት ለማወቅ እየተተራመሱ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ተቋማቱ አብዛኞቹን በተለይም ከ50 ዓመት በላይ የሆናቸውን ሠራተኞች ዕረፍት እንዲወጡና የተወሰኑ ሠራተኞችም ከቤታቸው ሆነው እንዲሠሩ ካደረጉ በኋላ፣ ‹‹አልተመደባችሁም›› ማለታቸው ሠራተኞች አቤቱታ አቅርቦ የመጠየቅ መብታቸውን እንዳይጠቀሙ የማድረግ ሴራ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
የተወሰኑ ዕረፍት ላይ በመሆናቸው ከከተማ ውጪ ያሉ በርካታ ሠራተኞችን መብትም የሚመለከት በመሆኑ፣ እስኪመለሱ ድረስ መታገድ እንዳለበትም አክለዋል፡፡ ምድቡ እንዴት እንደተሠራና ለምን ይህ ወቅት እንደተመረጠ እንዳልገባቸው የሚናገሩት ሠራተኞቹ መንግሥት ሠራተኛ እንዳይቀነስ በአዋጅ ከማሳወቁም በላይ፣ እንደ መሥፈርት ተወስዶ ያልተመደቡት ‹‹በነጥብ ተበልጠው›› የሚል ምክንያት መሆኑ እጅግ የሚያስገርምና የሚመለከተው አካል ትኩረት ሰጥቶ ሊያየው እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡
ከሥራ መታገድ ወይም አለመመደብ ካለባቸውም በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ሳይሆን፣ ምክንያቱ በሚገባ ተብራርቶ መሆን አለበት ብለዋል፡፡ ግልጽነት በጎደለው አሠራር ሳይሆን ቀደም ብሎ ወይም ይህ ወረርሽኙ ሲያልፍ መሆን ሲገባው፣ በችግር ላይ ችግር መፍጠር ኃላፊነትን መዘንጋት ወይም ለዜጎች አለማሰብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እነሱም እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የዚህ ወረርሽኝ ሥጋትና ተከታይ ችግሮችን ተጋሪ መሆናቸው ታስቦ፣ የከተማ አስተዳደሩ ወይም መንግሥት መፍትሔ እንዲሰጣቸውና አመዳደቡም እንዲጣራላቸው ጠይቀዋል፡፡
የተቋማቱ ሠራተኞች ከሥራ ገበታቸው መታገዳቸውን በተመለከተ የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት አስተዳደር ቢሮ፣ ኮርፖሬሽን፣ ዲዛይን ጽሕፈት ቤትና ግንባታ ኢንተርፕራይዝ ኃላፊዎችን ለማግኘትና ማብራሪያ እንዲሰጡ ለማድረግ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡