በአሰፋ አደፍርስ
ምርጫ ዓይነቱ እጅግ ብዙ ነው፡፡ ምርጫ ከአማራጭ ነገሮች ውስጥ ግለሰብም ይሁን ማኅበረሰብ የሚወደውን፣ የሚያፈቅረውን፣ የሚግባባውን፣ የሚጥመውንና አርሶ ሊያመርት አዋጭ መስሎ የሚታየውን፣ ኤላ ቆፍሮ ውኃ አገኝበታለሁ ብሎ ያመነበትን አካባቢ፣ ላግባት፣ ላግባው ብላ ወይም ብሎ ያሰቡትን መምረጥና የመሳሰሉትን የሚያጠቃልል ሁሉ ምርጫ ይባላል። ይህ የኖረና የሚኖርም የተፈጥሮ ልምድ ሆኖ እዚህ ያደረሰን ነው።
የተፈጥሮ ሁኔታ ሊሆን የቻለበት ምክንያት የሰው ፍጡር ብቻ ሳይሆን፣ እንስሳትም ጭምር የሚያደርጉት ጉዳይ ሆኖ እዚህ ደርሷል። ለምሳሌ እንስሳትን በሩቁ ቆመን ስንመለከት በግራ በኩል ደረቅ ሜዳ፣ በቀኝ በኩል ለግጦሽ የሚሆን የለመለመ ሳር አለ እንበል፡፡ ይህንን ሳር ቢያዩ ላሞች፣ ፈረሶች፣ በጎችና የመሳሰሉት ወደ ለምለሙ ያመራሉ፡፡ ይህም ምርጫ መሆኑ ነው። አሳማና ለወገኑ የማያስብ ሆዳም ደግሞ ወደ ግብስብሱ ያመራል፡፡ ይህም ምርጫ መሆኑ ነው። አንበሳ፣ ነብርና የመሳሰሉት ደግሞ ሥጋ ነኮች ወዳሉብት መሄድ ምርጫቸው ይሆናል።
ሰዎች መቼና ለምን መሪ ፈለጉ? የሰው ልጆች ከእንስሳት የተለየ ዕውቀት ስለነበራው ዝም ብለን ከመንጋጋት፣ ከመሀላችን የተሻሉትን መርጠን መንገዱን ይምሩን በማለት ነበር የጀመሩት፡፡ ነገር ግን እንደሚታወቀው የሰው ልጅ ብልህ ነውና ወዲያውኑ አንዱ አዛዥ አንዱ የታዛዥነት መልክ ይዞ ሁኔታውን በመለወጡ፣ እንዲያውም ከሰማይ የመጣልን ሥልጣን ነው በማለት አንዱ አንዱን ማዘዝና ማስገበረ ጀመረ። ጦር ማከማቸትና ጉልበተኛው ጉልበት የሌለውን ማጥቃት ትልቁ ተግባር ሆነ። ይህም እስከ እ.ኤ.አ. 1762 ጆን ጃክ ሩሶ በግልጽ እንዳስቀመጠው፣ ‹‹የግል ነፃነታችንን፣ ሰላምና ጤንነታችን እንዲጠበቅ ብለው የጥንት ወገኖቻችን ያመጡት በጎ የአገዛዝ ሥልት ተለውጦ ወደ ባርነት ገባን፡፡ እንደኛው ለተፈጥረ ፍጡር እየተገዛን ነፃነታችንን ስላጣን መንገድ መፈለግ አለብን፣ ሲሻን የምንሾመው ሲሻን የምንሽረውን ራሳችን መመረጥ አለበን፤›› ብሎ ያቀረበው ፍልስፍና ብዙም ሳይቆይ ባሰበውና በወጠነው መሠረት ይዞለት በ26 ዓመታት ውስጥ ተሳካለት።
ይህ ሐሳብ ከተነገረ ከ26 ዓመታት በኋላ አዲሷ አገር አሜሪካ እ.ኤ.አ. በ1788 ዓ.ም ከእናት አገሯ እንግሊዝ አምፃና ተዋግታ በአሸናፊነት የራሷን መንግሥት በማቋቋም፣ የመጀመሪያውን የራስን መሪ መርጦ በራስ መተዳደርን ጀመረች። ይህም ጅማሮ አድሮ ውሎ እየተስፋፋ ሄዶ መላውን ዓለም በማዳረስ ወደ ኢትዮጵያም እየደረሰ በሚመስል ሁኔታ እየመጣ ነው። መቼም በግብር ባይታይም እየተሞከረ ነው፡፡ ሁሌም ያው ከላይ ያለው መሪ ብቻ አድራጊ፣ ፈጣሪና ወሳኝ በመሆኑ ነው። ይሁን እንጂ ማንም ይምራ ማን አገሩን ሰላም አድርጎ፣ ተደማምጦና ተግባብቶ መሥራት ከቻለ ያ የተፈለገው አመራር ውሎ ይደር እንጂ ይመጣል ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ ሁሉ ሊሆን የሚችለው ግን በአገር ውስጥ ሰላም ሲኖር ብቻ ነው። ሰላም ለጦርነት ብቻም አይደለም፡፡ በአገር ላይ ረሃብ፣ በሽታ፣ ቸነፈርና የእግዜብሔር ቁጣን የመሳሰሉት በሚከሰቱበት ጊዜ ለሕዝቡ አስባለሁ ባይ የፖለቲካ ሰውም ሆነ ሌላው፣ ባለው አቅምና ችሎታ አገሩን ከመከራ ለማዳን ይሯሯጣል እንጂ፣ አሁን ባለንበት በሠለጠነው ዘመን ሥልጣን ለማግኘት ብሎ መሯሯጥ በድንጋይ ዳቦ ጊዜ ከሰማይ ተወርውረን የመጣን ነን ከሚሉት ነባር መሪዎች የከፋና ለአገር አለማሰብን፣ በወገን ላይ የራስን ጥቅም ማስቀደምን፣ ጭካኔና መጪውን መከራ ያለ ማገናዘብን፣ ለመሪነትም ብቁ አለመሆንንና የሥልጣን ጥመኝነትን ያሳያል።
በኢትዮጵያ ውስጥ የፖለቲካ መሪዎች ነን ብለው ምርጫ ዛሬ ካልሆነ የሚሉ፣ ሕዝብ ለማገልገልና መልካም አመራር ለመስጠት የቸኮሉ ሳይሆኑ የሕዝብን ሥቃይ ለማየት የሚጎመጁ ነው የሚመስሉት። ምክንያቱም ሕዝብ ለማገልገል የተዘጋጀ ቡድንም ሆነ ግለሰብ መጀመሪያ የአገርን የሰላም ሁኔታ ያገናዝባል፡፡ ሰላም ከሌለ ሰላም እንዴት መስፈን እንዳለበት ሥልጣን ላይ ካለው አመራር ጋር በመመካከርና በመተባበር ሁሉም ነገር ከሰከነ በኋላ፣ ከሕዝብ ጋር በመስማማት ያለውን መንግሥት በዘመኑ ሁኔታ ለመወዳደር ይዘጋጃል፡፡ በሕዝብ ድምፅ ምርጫውን ካሸነፈ በተራው ይመራል እንጂ፣ አገር ቀውጢ ሆና እኔ ካላልኩ በሚል ትምክሀት የማወናበድ ዘመቻ አንደኛ ሕዝብን እንደ መናቅ ይቆጠራል፡፡ ሁለተኛ እኔ ካልመራሁ ሁሉም ገደል ይግባ ዓይነት ሩጫን አስተዋዩ የኢትዮጵያ ሕዝብ በዝምታ የሚያልፈው ጉዳይ ስላልሆነ በማናለብኝነት የሚደረገው እሽቅድምድም በአጭሩ ቢቀጭ ጥሩ ነው፡፡ በኢትዮጵያዊያን ነባር ባህላቸውና እሴታቸው መሠረት አንዱ ለሌላው በማሰብና በመተባበር፣ የፖለቲካ ሥልጣን ጥመኞችም አገርን እንዳልነበረች ከማድረግ ተቆጥበው ወደ ልቦናቸው ቢመለሱ ይመረጣል።
አንድ ጣት ተበላሸ ተብሎ እንደማይጣል ሁሉ የፖለቲካ ሥልጣን ጥመኞች ሕዝቡን ቢያስከፉ እንኳ ወገን ናቸውና በይቅርታ ስለሚታለፉ፣ ሳይርቅ በቅርቡ ወደ ልቦናቸው ቢመለሱ የተሻለ ይሆናልና ያስቡበት። አሁን የሚያደርጉትን የእሽቅድምድም ዳንኪራቸውን እንዲያቆሙ፣ ለሕዝቡ በእውነት ለማገልገል ከሆነ በግብር እንዲያሳዩ የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንክሮ ይመለከታቸዋል።
ምርጫ አገር ሲኖር፣ ሕዝብ ሰላም አግኝቶ እንደ ልቡ ሲወጣና ሲገባና የዕለት ግብሩን መፈጸም ሲችል እንጂ፣ እንደታሰረ ነብር ከቤትህ አትውጣ ተብሎ በእግዜብሔር እጅ ያለን ሕዝብ ችግሩንና መከራውን እንዴት ይወጣው ይሆን ብሎ የመጣበትን መከራ አብሮ ከማሰብ ይልቅ እኔ ለምን አልሳተፍኩም፣ እኔ ለምን አልታወቅሁም በማለት ራስን ማስቀደም ነውር ነው፡፡ የሚደረገውን የሥልጣን ሽኩቻ በትዝብት የሚመለከተው ሕዝብ በቃኝ ብሎ፣ አንተ ለመሆኑ በሕይወትህ ምን ሠርተህና ምን አስተዋጽኦ አድርገህ ነው ዛሬ እኔን እመራለሁ ብለህ ግራ የምታጋባኝ ቢል መልሱ ምን ይሆን? ልብ በሉ!
በየትኛውም አገር ሰዎች ተገቢውን ሥራ በማከናወን ለአገራቸው አስተዋጽኦ አድርገው፣ የሕዝብን አዎንታ አግኝተው፣ ሕዝቡም ይህ የለፋልንና አበሮን የተንከራተተ፣ ችግር መከራችንን የሚያውቅ ነውና እርሱ ቢመራን ብሎ ራሱ ጠቁሞ ለምርጫ ሲያበቃ በመወዳደር ያሸነፈ ይመራል፡፡ የተሸነፈም አገሩን ያገለግላል እንጂ፣ ተሸነፍኩ ብሎ አኩርፎ አይቀመጥም፡፡ የተወዳደረውንም ደግፎት አብሮ ይሠራል እንጂ፣ ከሕዝብ ፍላጎት አፈንግጦ ሌላ ተግባር አይፈጽምም፡፡ በፖለቲካ ምኅዳሩ መስፋት በአቋራጭ ገብቶ በቴሌቪዥን ስለዘባረቀና ዕይን አግኝቶ በዚያ ስለታወቀ፣ ተሾሎክልኮ አንድ አገር ደርሶ ስለተመለሰ አገርን ይመራል ማለት አይደለም። አገር ለመምራት ተሞክሮ፣ በመስኩ ትምህርትና ልምድ ማስፈለጉንም መገንዘብ ያስፈልጋልና ይታሰብበት።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ከደግነቱና ከአስተዋይነቱ የተነሳ ሁሉንም በትዕግሥት ስለሚመለከትና ስለሚያሳልፍ፣ እንዲያው የተጫነው ሁሉ ማራገፊያ እንዳልሆነም ቢታወቅ መልካም ነው። የአገርን ሰላምና የሕዝብን ጤንነት ማገናዘብ ያልቻለ እንዴት ነው አገርን ሊመራ የሚሯሯጠው? ይህ የድንጋይ ዳቦ ዘመን አይደለምና የፖለቲካ መሪዎች ሕዝቡ ይታዘበናል በማለት አዙሮ ለማየት አንገት ይኑራችሁ። በሉ ልቦና ይስጣችሁ፣ ለአገርና ለወገን የሚያሰብ አዕምሮ ይስጣችሁ እያልኩ እሰናበታለሁ፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው ‹‹ከባቹማ እስከ ቨርጂኒያ›› በሚል ርዕስ ለአንባቢያን የቀረበ ግለ ሕይወትና የጉዞ ታሪክ መጽሐፍ ደራሲ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡