ዓርብ ሚያዝያ 16 ቀን 2012 ዓ.ም. ሕዝበ ሙስሊሙ ለአንድ ወር የረመዳን ፆም ሲጀምር፣ በአዲስ አበባ ከተማ በታላቁ አንዋር መስጊድ በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት በተላለፈው መመርያ መሠረት የእስልምና እምነት ተከታዮች ዝር አላሉም ነበር፡፡ በአካባቢው በንግድ ሥራ ላይ ከተሰማሩና ግብይት ለመፈጸም ከተገኙ ውስን ሰዎች በስተቀር ጭር ብሏል፡፡ የመስጊዱ በሮች ዝግ ከመሆናቸውም በላይ፣ ዘወትር ይታወቅ የነበረው የጁምዓ ፀሎትና ስግደት በቤት ውስጥ እንዲከናወን በመደረጉ የወትሮው እንቅስቃሴ አይታሰብም፡፡ የረመዳን ወር የፆምና የጸሎት በመሆኑ፣ በሕዝበ ሙስሊሙ ዘንድ በከፍተኛ ናፍቆት የሚጠበቅ ነው፡፡ ዘንድሮ ግን በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት የእምነቱ ተከታዮች በቤታቸው እንዲወሰኑ ተገደዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ፆሙን በማስመልከት ባስተላለፉት መልዕክት ነቢዩ መሐመድ ስለወረርሽኝ የተናገሩትን ቁርዓንን በመጥቀስ ሲያስረዱ፣ ‹‹በአንድ ሥፍራ ወረርሽኝ መነሳቱን ከሰማችሁ ወደዚያ ሥፍራ አትግቡ፣ ወረርሽኙ እናንተ ባላችሁበት ሥፍራ ከተከሰተ ደግሞ ከሥፍራው አትውጡ፤›› ያሉትን አስታውሰዋል፡፡ ብዙ ሰዎች ከሚሰበሰቡበት ቦታና እንቅስቃሴዎች ከሚደምቁት ሥፍራ መቆጠብ፣ ራስንም ሆነ ሌሎችን ከዚህ ወረርሽኝ ለመጠበቅ ያስችላል ሲሉም አክለዋል፡፡ ሕዝበ ሙስሊሙም የረመዳን ፆምን በዚህ መሠረት ነው የጀመረው፡፡ በምሥሉ ላይ በታላቁ አንዋር መስጊድ አካባቢ የሚገኙ ቴምርና መሰል ሸቀጦች መሸጫዎች ይታያሉ፡፡ ፎቶ፡- ታምራት ጌታቸው