በእሑድ ሚያዝያ 18 ቀን 2012 ዓ.ም. ዕትም ‹‹ወደ ኢትዮጵያ የገቡ መንገደኞች ከቫይረሱ ነፃ መሆናቸው በምርመራ ሳይረጋገጥ ከማቆያ ማዕከላት እንዳይወጡ ተወሰነ›› በሚል ርዕስ በወጣው ዘገባ ውስጥ በአባሪነት፣ ‹ኤካ ኮተቤ ሆስፒታል በአሁኑ ወቅት ሕክምና የመስጠት አቅሙ የመጨረሻ ደረጃ ላይ የደረሰ በመሆኑ የቅዱስ ጳውሎስ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል በኮሮና ቫይረስ ለተያዙ ሰዎች ብቻ የሕክምና አገልግሎት እንዲሰጥ በመወሰኑ፣ ሆስፒታሉ ነባር ታካሚዎችን ወደ ሌሎች የሕክምና ማዕከላት ለማዘዋወር ዝግጁ ሆኗል› የተባለው ስህተት መሆኑን አረጋግጠናል:: በአሁኑ ወቅት በኤካ ኮተቤ ሆስፒታል ለኮሮና ቫይረስ ታማሚዎች ተብሎ የተዘጋጀው አልጋ 109 የተባለውም ስህተት ነው:: የሆስፒታሉ አልጋ ብዛት 600 ሲሆን፣ በአሁኑ ጊዜ በኤካ ኮተቤ ሆስፒታል የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው የሚገኙት ሕሙማን 69 ብቻ መሆናቸውን ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል። ይህ ደግሞ በአጠቃላይ ከተዘጋጀው 600 አልጋ ሆስፒታሉ አገልግሎት መስጠት ከሚችለው 11.5 በመቶ ብቻ እንደሆነም ገልጿል። የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ምንም እንኳን በተወሰነ ደረጃ ለዚሁ አገልግሎት አመቺነቱ ታይቶ በተለየ ሕንፃ ላይ የኮቪድ 19 ሕሙማንን ለመቀበል ዝግጅት እያደረገ ቢሆንም፣ ሆስፒታሉ መደበኛ የሕክምና አገልግሎትን በነበረበት አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል:: መረጃውን በማሰባሰብና በማጠናቀር ረገድ ለተፈጠረው ስህተት ጤና ሚኒስቴርንና አንባብያንን ይቅርታ እንጠይቃለን::