የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቴዎድሮስ አሸናፊ ፋውንዴሽን በ25 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባውን የጎዳና ላይ ልጆች ማቋቋሚያ ማዕከል ተረከበ፡፡
በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ የተገነባው ማቋቋሚያ ማዕከል ወጪው ሙሉ በሙሉ በፋውንዴሽኑ የተሸፈነ ሲሆን፣ 2‚000 ታዳጊዎችን የማስተናገድ አቅም እንዳለው ተገልጿል፡፡
ማዕከሉ 280 የመኝታ ክፍሎች፣ የመጀመርያ ዕርዳታ መስጫ ክሊኒክ፣ ሁለት የአስተዳደር ቢሮ መገልገያዎች፣ አንድ የመመገቢያና የቴሌቪዥን መመልከቻ ክፍል አለው፡፡ እንዲሁም 36 የቁም ገላ መታጠቢያ፣ ስምንት መፀዳጃ ቤቶችና 16 የልብስ ማጠቢያ ገንዳዎች አሟልቶ ይዟል፡፡
የፋውንዴሽኑ ሊቀመንበር አቶ ቴዎድሮስ አሸናፊ ማዕከሉን፣ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሙሉጌታ ተፈራ አስረክበዋል፡፡
ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻቀበ የመጣው የጎዳና ተዳዳሪ ልጆች ብዛት አሳሳቢ የማኅበራዊ ችግር እንደሆነ ተነግሯል፡፡ በቅርቡ ለተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ የጎዳና ላይ ልጆች ተጋላጭ መሆናቸው ችግሩን የበለጠ አስከፊ እንደሚያደርገው ተጠቁሟል፡፡
ይህንን ማኅበራዊ ቀውስ በመመልከት በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተጀመረውን የጎዳና ላይ ልጆች ማቋቋሚያ ፕሮጀክት ለመደገፍ፣ ፋውንዴሽኑ 2‚000 ታዳጊዎችን ሊያስተናግድ የሚችል ማቋቋሚያ ማዕከል ገንብቶ ማስረከቡን አስታውቋል፡፡
በርክክቡ ሥነ ሥርዓት ላይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከተለያዩ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ጋር በመተባበር ጎዳና ላይ የወደቁ ዜጎችን መልሶ በማቋቋም ላይ እንደሆነ አቶ ሙሉጌታ ተናግረዋል፡፡ አስተዳደሩ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከሚደገፉ ስምንት አገር በቀል ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ጋር በመተባበር 2‚000 ዜጎችን ከጎዳና ላይ ማንሳቱን አስረድተዋል፡፡ ኤልሻዳይ ሪሊፍ ኤንድ ዲቨሎፕመንት የተሰኘው ግብረ ሰናይ ድርጅት 1‚200 ዜጎችን ከጎዳና ላይ እንዳነሳም ገልጸዋል፡፡
አስተዳደሩ 300 የሚሆኑ ዜጎችን አቃቂ በሚገኘው መልሶ ማቋቋሚያ እንዳስገነባ ጠቁመው፣ በአጠቃላይ በሁለት ወራት ውስጥ 3‚500 ዜጎችን ከጎዳና ላይ ማንሳት እንደተቻለ ገልጸዋል፡፡ በቀጣይ አስተዳደሩ ከመቄዶኒያ፣ ስምንት መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች፣ ኤልሻዳይ ሪሊፍ ኤንድ ዲቨሎፕመንትና በራስ አቅም በድምሩ 11‚000 ዜጎችን ከጎዳና ላይ ለማንሳት እንደታቀደ አስረድተዋል፡፡
‹‹ቴዎድሮስ አሸናፊ ፋውንዴሽን ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ ላስተላለፉት ጥሪ አፋጣኝ ምላሽ ሰጥቷል፤›› ያሉት አቶ ሙሉጌታ፣ ፋውንዴሽኑን ገንብቶ ያስረከበው ማዕከል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለጀመረው የጎዳና ላይ ልጆችን የማንሳት ፕሮጀክት ትልቅ ዕገዛ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
ማዕከሉ ታዳጊዎችንና ወጣቶችን መልሶ ለማቋቋም የተለያዩ ሥልጠናዎች ለመስጠት እንደሚጠቅም ገልጸዋል፡፡ ለወጣቶቹ የሥነ አዕምሮና የሙያ ሥልጠናዎች በመስጠት ወደ መደበኛ ሕይወት እንዲገቡ እንደሚደረግ አስረድተዋል፡፡
የፋውንዴሽኑ ሊቀመንበር የመልሶ ማቋቋሚያ ማዕከሉ ግንባታ የተጠናቀቀው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በተስፋፋበት ወቅት በመሆኑ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ኅብረተሰቡና መንግሥት ለሚያደርጉት ወረርሽኙን የመቆጣጠር ጥረት ዕገዛ ያደርጋል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ መንግሥት የጀመረውን የጎዳና ላይ ልጆች የማቋቋም ጥረት የንግዱ ማኅበረሰብ፣ የሲቪል ማኅበረሰብና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ዕገዛ አስፈላጊ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡