ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ከሱዳን አቻቸው ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሐምዶክ ጋር፣ የሁለቱ አገሮችን ድንበር በፍጥነት ማካለል በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መከሩ።
የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ባወጣው መረጃ እንዳመላከተው ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ከሱዳን አቻቸው አብዱላ ሐምዶክ ጋር በስልክ በዋናነት የተወያዩት፣ ሁለቱን አገሮች የሚያዋስነው ድንበር በፍጥነት ስለሚከላልበት ሁኔታና ሌሎች የሁለትዮሽ የትብብር ጉዳዮችም ተነስተዋል።
በውይይታቸውም የድንበር ማካለሉን ተግባር በፍጥነት ማስጀመር እንዲቻል የድንበር ማካላል የቴክኒክ ኮሚቴ እንዲቋቋም፣ በሁለቱ አገሮች መሪዎች ውይይት ተነስቶ መግባባት እንደተደረሰበት የሱዳን መንግሥት ያወጣው መግለጫ ያመለክታል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ በበኩላቸው የኢትዮጵያና የሱዳን ጉርብትናና ጠንካራ ወዳጅነትን በውይይቱ ወቅት እንዳነሱ፣ ይህም መልካም ግንኙነት በሁለቱ አገሮች የድንበር አካባቢዎች ውጥረት እንዳይነሳ ለመከላከል እንደሚረዳ መግለጻቸውን ከመረጃው ለማወቅ ተችሏል።
በሁለቱ አገሮች ድንበር የሚነሳ ማንኛውም ጉዳይና አለመግባባት በአገሮቹ የፖለቲካ መሪዎችና የጦር አመራሮች ቀጥተኛና ግልጽ ውይይት መፈታት እንደሚኖርበት መስማማታቸውን፣ የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ውይይቱን አስመልክቶ ያወጣው መግለጫ ያስረዳል።
ሁለቱ መሪዎች በስልክ ከመወያየታቸው ጥቂት ቀናት አስቀድሞም የኢትዮጵያ በመከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹም ጀኔራል አደም መሐመድ የተመራ ከፍተኛ ወታደራዊ ልዑክ ከሱዳኑ ጠቅላይ ሚኒስትር፣ እንዲሁም የሱዳን መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹም ሌተና ጄኔራል መሐመድ ኦስማንና የሱዳን ወታደራዊ ደኅንነት ኃላፊ ሌተና ጄኔራል ያሲር መሐመድ በተገኙበት መምከራቸውን ይኸው መረጃ ያመለክታል።
በኢትዮጵያና በሱዳን መካከል ከሺሕ በላይ ኪሎ ሜትሮችን የሚያካልል ድንበር እስከ ዛሬ ድረስ በሕጋዊ መንገድ አለመካለሉ የሚታወቅ ሲሆን፣ በተለይ ባለፉት አሥራ አምስት ዓመታት ገደማ ከሱዳን በሚያዋስነው አማራ ክልል ውስጥ በሚገኙ የሁለቱ አገሮች ሠራዊቶች መካከል በየጊዜው የሚከሰት አለመግባባት መኖሩ ይታወቃል፡፡