ሰኞ ግንቦት 10 ቀን 2012 ዓ.ም. በትግራይ ክልል መቐለ ከተማ በሚደረገው የኢትዮጵያ የፌዴራሊስት ኃይሎች ጥምረት መድረክ ላይ ለመሳተፍ በመሄድ ላይ የነበሩ የጥምረቱ አምስት አባላት፣ ከቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት ተወስደው መታሰራቸው ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎችንና ሕገ መንግሥቱን የጣሰ መሆኑን የትግራይ ክልል መንግሥት አስታወቀ፡፡
የትግራይ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ባወጣው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ የጥምረቱ አባላት ማንነታቸው ባልታወቀ የፀጥታ ኃይሎች ግንቦት 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ 8፡45 ሰዓት ላይ በቁጥጥር ሥር ውለው የታሰሩት የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ንቅናቄ (አነን) ሊቀመንበር አቶ መሳፍንት ሽፈራው፣ የኢዲዩኅ አባል አቶ ገብሩ በርሄ፣ የነፃነት ለአንድነት አባል አቶ ተሻገር አረጋ፣ የኢሴዴፓ አባል መዲና ይማምና የኢዜአን ሊቀመንበር አቶ ጉዑሽ ገብረ ሥላሴ ናቸው፡፡
የኮሮና ቫይረስ ምርመራ እንደሚደረግላቸው ተነግሯቸው ከቦሌ ኤርፖርት የተወሰዱት የጥምረቱ አባላት የት እንደታሰሩ እንደማያውቅ የገለጸው ቢሮው፣ ይህ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመሆኑ አባላቱ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ ጠይቋል፡፡ አባላቱ በሕገ መንግሥቱ የተፈቀደላቸውን የመደራጀት መብት ተጠቅመው በፈለጉት የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ የመሳተፍና የመደራጀት መብት ያላቸው ቢሆንም መብታቸውን መነፈጋቸውን ጠቁሟል፡፡ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ (17) የተጎናፀፉት ነፃ የመሆን መብታቸው፣ እንዲሁም በአንቀጽ 18 ተደንግጎ የሚገኘውና ለማንኛውም ኢትዮጵያዊ ሊከበርለት የሚገባው ሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደ ተፈጸመባቸውም ቢሮው ገልጿል፡፡ የፌዴራል መንግሥት ተገቢውን የዕርምት ዕርምጃ በመውሰድ የታሰሩትን የጥምረቱ አባላት እንዲፈታቸው አሳስቧል፡፡ ዜጎች በነፃነት እንዳይንቀሳቀሱ የሚደረገው ክልከላና አፈናም እንዲቆም ጠይቋል፡፡
የትግራይ ክልል መንግሥት ያቀረበውን ተቃውሞና ታስረዋል ያላቸው የፌዴራሊስት ኃይሎች አባላት ለምን እንደ ታሰሩና የት እንደ ታሰሩ መረጃ ለማግኘት ሪፖርተር ያነጋገራቸው የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄኔራል እንደሻው ጣሰው፣ ከሌላ ጥምር ኃይል ጋር እየተሠራ በመሆኑ ሰሞኑን እንደሚያሳውቁ ከመናገር ውጪ ያሉት ነገር የለም፡፡
ግለሰቦቹ ከግንቦት 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ልደታ በሚገኘው የሕንፃ ኮሌጅ አካባቢ ለየብቻቸው መታሰራቸውንና ቤተሰብም ሆነ ሌላ አካል እየጠየቃቸው እንዳልሆነ ተጠቁሟል፡፡ ቤተሰቦቻቸው ለስብሰባ መቐለ እንደሄዱ እንጂ መታሰራቸውን ስለማያውቁ፣ መንግሥት የተጠረጠሩበት የወንጀል ድርጊት ካለም እውነታውን ነግሮ ቢያንስ እንዲጠይቋቸው ጠይቀዋል፡፡ እንዲሁም ከእስር እንዲለቀቁ ጠይቀው፣ መታሰራቸውን ከማኅበራዊ የትስስር ገጾች ማንበባቸውን የተወሰኑት የታሳሪዎች ቤተሰቦች ተናግረዋል፡፡