ለአማራ ክልል ምክር ቤት ተጠሪ የሆነው ጥረት ኮርፖሬት የቀድሞ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታደሰ ካሳ ከሌሎች ተከሳሾች ጋር በተከሰሱበት የሙስና ወንጀል ክስ፣ በስምንት ዓመታት እስራትና በ20 ሺሕ ብር እንዲቀጡ የክልሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡
ከአንድ ሳምንት በፊት ከአቶ በረከት ስምዖን ጋር በተከሰሱበት የመደበኛ ወንጀልና የሙስና ክስ፣ የስምንት ዓመታት እስርና 15 ሺሕ ብር እንዲቀጡ በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት እንደተወሰነባቸው ይታወሳል፡፡ በመሆኑም አቶ ታደሰ ካሳ በሁለቱም መዝገቦች የ16 ዓመታት እስርና የ35 ሺሕ ብር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባቸዋል፡፡
በጥረት ኮርፖሬት ሥር በሚገኙ ኩባንያዎች በተለያዩ ኃላፊነት ላይ ይሠሩ የነበሩትና ከዓመት በፊት የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል ተብለው ክስ ተመሥርቶባቸው የነበሩት አቶ ታደሰ ካሳ፣ ወ/ሮ ቤተልሔም ብርሃኑ፣ ወ/ሮ እየሩሳሌም ብርሃኑ፣ ወ/ሮ ዓይናለም ኃይለ ልዑል፣ አቶ ግርማቸው ዘውዱ፣ ፍኖተ ሰላም ተክሌ (በሌሉበት) እና ዕፀገነት ጌታቸው (በሌሉበት) ነበሩ፡፡
ክሱን ሲመረምርና ሲያከራክር የከረመው የባህር ዳርና አካባቢው ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሐሙስ ግንቦት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው የቅጣት ውሳኔ አቶ ታደሰ በስምንት ዓመታት ከአምስት ወራትና 20 ሺሕ ብር፣ ወ/ሮ ቤተልሔምና ወ/ሮ እየሩሳሌም እያንዳቸው ሦስት ዓመታት እስርና ሰባት ሺሕ ብር፣ ወ/ሮ ዓይናለም በሁለት ዓመታት እስርና አራት ሺሕ ብር፣ አቶ ግርማቸው በሁለት ዓመታት ከዘጠኝ ወራት እስርና ስድስት ሺሕ ብር እንዲቀጡ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡
በሌሉበት ጉዳያቸው ሲታይ የነበሩት ፍኖተ ሰላምና ዕፀገነት እያንዳንዳቸው በሦስት ዓመታት ከሰባት ወራት እስርና አሥር ሺሕ ብር እንዲቀጡ ወስኖ፣ ፖሊስ ካሉበት ይዞ እንዲያስፈጽም ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ግንቦት 10 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው የጥፋተኝነት ውሳኔ መዝገብ ተካተው የነበሩትን አቶ ምትኩ በየነንና ሐጂ ሁሴን አህመድን በነፃ አሰናብቷቸዋል፡፡ ወ/ሮ ቤተልሔም፣ ወ/ሮ እየሩሳሌም፣ ወ/ሮ ዓይናለም፣ አቶ ግርማቸው የተጣለባቸውን የእስራት ቅጣት በሁለት ዓመታት ገደብና በ50 ሺሕ ብር ዋስትና ከእስር እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡