➤የሊዝ ክፍያ ባልፈጸሙ ላይ ቅየጣትና ወለድ ክፍያ እንዲነሳ ተወስኗል
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ ቅዳሜ ግንቦት 29 ቀን 2012 ዓ.ም. ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ መሬት በሊዝ ወስደው ግንባታ ላልጀመሩ ባለሀብቶች የአንድ ዓመት ማራዘሚያ እንዲሰጣቸው ወሰነ።
ከዚህ በተጨማሪም የሊዝ ክፍያቸውን ያልፈጸሙ ባለይዞታዎች ላይ የሚጣለው የቅጣትና የወለድ ክፍያዎችም ቀሪ ሆነው ፍሬ የሊዝ ክፍያውን ብቻ እንዲከፍሉ ወስኗል።
የከተማ አስተዳደሩ እነዚህንና ሌሎች ውሳኔዎችን ያሳለፈው በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት የከተማዋ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መዳከሙን ከግምት በማስገባትና የበኩሉን ማነቃቂያ ድጋፍ ለማድረግ መሆኑ ታውቋል።
ከከተማ አስተዳደሩ መሬት በሊዝ ሕጉ መሠረት የወሰዱና በ18 ወራት ውስጥ ምንም ዓይንት ግንባታ ያልጀመሩ ከሆነ መሬቱን ይነጠቃሉ።
ይሁን እንጂ ካቢኔው ከቫይረሱ ስርጭት ጋር በተገናኘ የኢኮኖሚ መዳከም በመፈጠሩ መሬት የወሰዱ አልሚዎችን የግድ ወደ ግንባታ እንዲገቡ ማስገደድና ይህንን ባለደረጉት ላይ የሊዝ ውሉን ማቋረጥ ተገቢ አለመሆኑን በመገምገም፣ ግንባታ ያልጀመሩ አልሚዎች የአንድ ዓመት ማራዘሚያ እንዲያገኙ ወስኗል።
ጉዳዩ የሚመለከታቸው ባለይዞታዎች የውሳኔው ተጠቃሚ ለመሆን የሚጠበቅባቸው የግንባታ ፈቃዳቸውን ማሳደስ ብቻ ሲሆን፣ የግንባታ ፈቃዳቸውም ያለ ቅጣት እንዲታደስ ተወስኖላቸዋል።
ከዚህ በተጨማሪም ከሪል ስቴት አልሚዎች ውጪ ያሉና የመሬት ሊዝ ክፍያቸውን ባልፈጸሙት ላይም ቅጣትና ወለድ እንዲነሳ ካቢኔው መወሰኑን ለማወቅ ተችሏል።
በዚህም መሠረት በቀጥታ በሊዝ ሕጉ መሠረት መሬት በሊዝ የወሰዱ፣ አግባብ ባለው አካል የይዞታ ማረጋገጫ አግኝተው ይዞታቸው በሊዝ ሥርዓት እንዲስተናገድ የተወሰነላቸው አልሚዎች እንዲሁም የመኖሪያ ባለይዞታዎች ባልከፈሉት የሊዝ እዳ ላይ ቅጣትና ወለድ ክፍያ እንዳይጣልባቸው ተወስኗል።
በዚህ ምክንያት በክስ ሂደት ላይ የሚገኙ አልሚዎችም ከቅጣቱና ከወለድ ክፍያው 30 በመቶ ተነስቶላቸው እንዲከፍሉ ተወስኖላቸዋል።