የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኢትዮጵያ አዲስ አምባሳደር ለመሾም ሴኔቱ እንዲያፀድቅላቸው መላካቸው ተሰማ፡፡ አዲሷ ተሿሚ አምባሳደር ህንዳዊ አሜሪካዊቷ ጊታ ፓሲ ሲሆኑ፣ እንደ እ.ኤ.አ. ከሴፕቴምበር ከ2017 ጀምሮ በሥራ ላይ የነበሩትን አምባሳደር ማይክል ሬይነር እንደሚተኩ ከዋይት ሐውስ ፕሬስ ክፍል ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
የ58 ዓመቷ አምባሳደር ፓሲ በአሁኑ ወቅት የስቴት ዲፓርትመንት የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ፀሐፊ ምክትል ዋና ኃላፊ ናቸው፡፡ ከዚህ ቀደም በቻድና በጂቡቲ የአሜሪካ አምባሳደር በመሆን ማገልገላቸው ተመልክቷል፡፡
አሜሪካን በተለያዩ የዲፕሎማቲክ ተልዕኮዎች ማገልገላቸው የሚነገርላቸው አምባሳደር ፓሲ፣ በስቴት ዲፓርትመንት ውስጥም የአፍሪካ ጉዳዮች ዲፓርትመንት ዳይሬክተር ሆነው በመሥራት ይታወቃሉ፡፡ በባንግላዴሽ ዳካና በጀርመን ፍራንክፈርት የአሜሪካ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮን ምክትል ኃላፊ በመሆን መሥራታቸው ታውቋል፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት ኃላፊነቶች በተጨማሪ በስቴት ዲፓርትመንት በፓኪስታን፣ በአፍጋኒስታንና በባንግላዴሽ ቢሮ የአፍጋኒስታን ዴስክ ኦፊሰር ሆነው ከመሥራታቸውም በላይ፣ በህንድና በጋና የአሜሪካ ኤምባሲዎች የፖለቲካ ኦፊሰር በመሆን ማገልገላቸውን የዋይት ሐውስ ፕሬስ ክፍል አስታውቋል፡፡
ፕሬዚዳንት ትራምፕ ሰሞኑን ለስምንት አገሮች አዳዲስ አምባሳደሮችን ለመሾም ለሴኔቱ የላኩ ሲሆን፣ ከእነዚህ አገሮች መካከል አንደኛዋ ኢትዮጵያ ናት፡፡ ኢትዮጵያና አሜሪካ በይፋ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የጀመሩት እ.ኤ.አ. በ1903 ነበር፡፡