በተመስገን ተጋፋው
በጨቅላ ዕድሜያቸው ሲደፈሩ ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡ በቅጡ እንኳን ሳይቦርቁ ለጥቃት ሰለባ መሆናቸው በጤናቸው ላይ ትልቅ ችግር ፈጥሯል፡፡ የልጅነት ህልማቸውን ዕውን ሳያደርጉ መቅረታቸው በሕይወታቸው ላይ ተስፋ እንዲቆርጡ አድርጓቸዋል፡፡
ከዚያም አልፎ ራሳቸውን ከማኅበረሰቡ እንዲያገሉ ተገደዋል፡፡ በቤተሰብ ፍላጎትና ጫና ሴት ልጆች ያለ ዕድሜያቸው ወደ ትዳር እንዲገቡ መገደዳቸው ችግሩ ይበልጥ እንዲባባስ መንገድ ከፍቷል፡፡
አብዛኛውን ጊዜ ለፆታዊ ጥቃት ተጋላጭ የሆኑት የገጠር ሴት ልጆች ቢሆኑም፣ አሁን ላይ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች ፆታዊ ጥቃት እየተበራከተ ስለመምጣቱ እየተነገረ ነው፡፡
መልካም ወንድም፣ አባት አጎት ጓደኛ ቢኖሩም፣ በእነዚሁ ተደፈረች ወይም ተደፈረ ብሎ መናገር ነውር በሆነበት ማኅበረሰብ ውስጥ፣ አሁን እየተፈጠረ ያለውን ችግር ስፋት ለመገመት ቢያዳግትም፣ በአንዳንድ ቤተሰብ፣ በተቋማትና በጎረቤት አማካይነት የተለያዩ ፆታዊ ጥቃቶች እየተፈጸመ ስለመሆኑ ለመንግሥት አካላት ጥቆማ እየደረሰ ነው፡፡ አካላት ሴት ልጆች ይደፈራሉ፡፡ ወንዶችም የግብረሰዶም ሰለባ እየሆኑ ነው፡፡ በተለይ ኮቪድ 19 በኢትዮጵያ ከገባ ወዲህ ቤተሰብ በአንድ ቤት ታስሮ መቀመጡ፣ ለችግሩ እንደ አንድ ምክንያት ይነሳል፡፡ የከተማ ልጆች በትምህርት ሰበብ የዋይፋይ (ኢንተርኔት) ተጠቃሚ መሆናቸው ያልተገባውን ሁሉ እንዲያዩ ዕድል መፍጠሩ፣ የራሱን ጫና ሲያሳድር፣ ባልና ሚስት ሙሉ ቀን አብረው በመዋላቸው በሚፈጠር የተግባቦት ችግር ለፀብ እየተደረጉ እንደሆነም ይሰማል፡፡
ችግሩን ለመቅረፍ መንግሥት የተለያዩ አሠራሮችን ዘርግቶ እየሠራሁ ነው፡፡ ቀድሞ የነበረውና በቅጡ ያልተቀረፈው ችግር አገርሽቷል፡፡ ፍትህ ቶሎ አለማግኘትን ጨምሮ ችግሩ ከተከሰተ በኋላ በቤተሰብ ላይ የሚደርሰው ሃፍረትና ጫና እንዲሁም ራስን ማግለል ችግሩን ያባብሰዋል፡፡ እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ መንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት እየሠሩ ከሚገኙት ጋንዲ ሆስፒታል አንዱ ነው፡፡
የጋንዲ ሆስፒታል የተቀናጀ የሴቶችና ሕፃናት እንክብካቤና የአንድ መስኮት አገልግሎት ዘርፍ ባለሙያ ሲስተር ማንጉዳይ ሰይፉ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አስገድዶ መድፈር የደረሰባቸው ሴቶችና ሕፃናት አስፈላጊውን የሕክምና ክትትልና ተገቢውን ፍትሕ እንዲያገኙ ፖሊስ፣ ዓቃቤ ሕግና የሕክምና ባለሙያዎች አንድ ላይ በመሆን እየሠሩ ነው፡፡
ከ18 ዓመት በታች የሚገኙ ሕፃናት በተደፈሩ በ72 ሰዓት ውስጥ ወደ ሕክምና ከመጡ የኤችአይቪ ኤድስ፣ የአባላዘር፣ የእርግዝና መከላከያ መድኃኒቶችን እንደሚያገኙና የጉበትና የሽንት ምርመራ ይደረግላቸዋል፡፡ ከ18 ዓመት በላይ የሚገኙ ሴት ልጆች ወደ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ሪፈር ይጻፍላቸዋል፡፡
በግብረ ሰዶም ጥቃት የደረሰባቸውና ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ወንድ ልጆችም የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በላይ ሲሆን ደግሞ ወደ ሚመለከተው ሆስፒታል ሪፈር እንደሚደረግላቸው ሲስተር ማንጉዳይ ተናግረዋል፡፡
ከአስገድዶ መድፈር ጋር ተያይዞ ያረገዙ ልጆችም ካሉ ጥቃቱን ያደረሰው ሰው በሕግ እንዲያዝ ተደርጎ እርግዝናው የሚቋረጥ ሲሆን፣ እርግዝናውን ለማቋረጥ ችግር ይፈጥራል ተብሎ ከታሰበም በሆስፒታሉ ላይ ተመላላሽ ክፍል ውስጥ ክትትል እንዲያደርጉ ተመቻችቷል፡፡ አካላዊና አዕምሯዊ ጤናቸውን ወደ ቀድሞው ለመመለስ በሆስፒታሉ በሚገኙ የሥነ ልቦና ባለሙያዎች ምክርና አስፈላጊው እንክብካቤም ይደረግላቸዋል፡፡
አስገድዶ መድፈር የደረሰባቸው ሴት ሕፃናት ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል፣ ጥሩነሽ ቤጀንግ ሆስፒታልና ጋንዲ ሆስፒታል በመሄድ የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኙ መመቻቸቱን ለሪፖርተር የገለጹት የአዲስ አበባ የሴቶችና ሕፃናት ቢሮ የሥርዓተ ፆታ ጉዳይ ማካተትና ማስረፅ ዳይሬክተር አቶ ፀሐዬ ብርሃኑ ናቸው፡፡
በየካቲት 2012 ዓ.ም. ብቻ ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ 150 ሕፃናት አስገድዶ መድፈር ደርሶባቸዋል፡፡ ከኮሮና ቫይረስ መከሰት ጋር ተያይዞም በመጋቢት ወር ላይ 101 ሴት ሕፃናት መደፈራቸውን የገለጹት፣ አቶ ፀሐዬ 11 ወንዶች ግብረ ሰዶም የተፈጸመባቸ ሲሆን፣ 27ቱ ደግሞ ኮሮና ቫይረስ ኢትዮጵያ ከመግባቱ በፊት መደፈራቸውን አስታውሰዋል፡፡
አስገድዶ መድፈር የደረሰባቸው 101 ሴት ሕፃናት በተለያዩ ማገገሚያ ቦታዎች ላይ ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛሉ፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞም አስገድዶ መድፈርን ለማስቀረት ከሁሉም ክልሎች ጋር በጋራ እየሠሩ መሆኑን፣ አሁን ላገረሸው ችግር ዋነኛ ምክንያቱ በኮቪድ 19 ምክንያት ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸው እንደሆነና ይህንንም ተገን በማድረግ ፆታዊ ጥቃት እየደረሰ መሆኑ ሁኔታውን አሳሳቢ እንደሚያደርገው አስታውሰዋል፡፡