እስከ ማክሰኞ 75 ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ 4,848 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል
የጤና ሚኒስቴር ሰኔ 16 ቀን 2012 ዓ.ም. ባወጣው ዕለታዊ መግለጫው፣ በ24 ሰዓት ውስጥ በተደረገው 3,775 የላቦራቶሪ ምርመራ 185 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ ተገኝቶባቸዋል፡፡ ይህም በኢትዮጵያ ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸውን ሰዎች ቁጥር 4,848 አድርሶታል፡፡
የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር) በዝርዝር እንደገለጹት፣ ቫይረሱ የተገኘባቸው 184 ኢትዮጵያውያንና አንድ የውጭ ዜጋ ሲሆኑ፣ የዕድሜ ክልላቸውም ከ3 ወር እስከ 80 ዓመት የሆኑ 47 ወንዶችና 138 ሴቶች ናቸው።
ከአዲስ አበባ 160 ሰዎች (ከእነዚህም 105 ሰዎች ተመላሾችና በማቆያ የነበሩ)፣ ከደቡብና ኦሮሚያ ክልል እያንዳንዳቸው 7፣ አፋር 4፣ ሶማሌና አማራ እያንዳንዳቸው 2፣ ትግራይ፣ ጋምቤላና ሐረሪ እያንዳንዳቸው 1 ሰው ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል፡፡ ከጠቅላላው የላቦራቶሪ ምርመራ ውስጥ 30 ናሙናዎች በአስክሬን ላይ የተደረገ ሲሆን፣ ቫይረሱ የተገኘበት አንድም የለም።
እስከ ማክሰኞ ድረስ በኢትዮጵያ 223,341 የላቦራቶሪ ምርመራ መከናወኑንና በቫይረሱ ከተያዙት 4,848 ሰዎች ውስጥ ያገገሙት 1,412 መድረሱን፣ በፀና የታመሙ ሰዎች ቁጥር 38 እንደሆነም ተገልጿል፡፡
ተተኳሪ ጉዳዮች
የኖቭል ኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ 19) ከቀላል እስከ ከባድ የመተንፈሻ አካል ሕመም የሚያስከትል የቫይረስ ዝርያ ሲሆን በበሽታው የተያዙ ሰዎች ትኩሳት፣ ሳል፣ የትንፋሽ መቆራረጥና የመተንፈስ ችግር ምልክቶች ይታይባቸዋል፡፡
በዓለም ጤና ድርጅት አገላለጽ፣ ኮሮና ቫይረስ የተለያዩ የቫይረስ ዓይነቶችን የያዘ የቫይረስ ቤተሰብ ነው፡፡ ይህ ቫይረስ በሰዎችና በእንስሳት ላይ በሽታን ያስከትላል፡፡ በሰዎች ላይ የሚከሰተው ኮሮና ቫይረስ የመተንፈሻ አካላትን በመጉዳት ከተራ ጉንፋን እስከ ከፍተኛ የመተንፈሻ አካል ችግር የሚያደርስ ነው፡፡
በሽታው በጠናባቸው ታማሚዎች ላይ ደግሞ እንደ ሳንባ ምች (ኒሞኒያ)፣ ከባድ የመተንፈሻ አካላት ሕመም የሚያሳይ ሲሆን የኩላሊት ሥራ ማቆምና ሞትን ሊያስከትል የሚችል በሽታ ነው፡፡
ኅብረተሰቡ ከዚህ በፊት ማንኛውንም በሽታ ለመከላከል ሲጠቀምባቸው የነበረውን የበሽታ መከላከያ መንገዶች ችላ ሳይልና ሳይደናገጥ አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪውን ያስተላለፈው የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት፣ የበሽታውን ሥርጭት ለመቀነስ ቀጥለው የተዘረዘሩትን መልዕክቶች እንዲተገበሩ ጥሪ አቅርቧል፡፡
- ሳል ወይም ትኩሳት ካለው ግለሰብ ቢያንስ ሁለት የአዋቂ ዕርምጃ ርቀት ያህል መራቅ፣
- እጅዎን በአግባቡ ሳይታጠቡ ዓይንና አፍንጫዎን አይንኩ
- ከሰዎች ጋር አይጨባበጡ፣
- እጅን በንፁህ ውኃና ሳሙና አዘውትረው ይታጠቡ፣
- ሰዎች ወደ በሚበዙባቸው ቦታዎች በተለይም የሕመም ስሜት ካልዎት አይሂዱ፣
- በሚያነጥሱበትና በሚያስሉበት ጊዜ አፍና አፍንጫዎን በሶፍት ወይም ክርንዎን አጥፈው በመጠቀም ወደ ሌሎች እንዳያስተላልፉ ይጠንቀቁ፣
- የተጠቀሙበትን ሶፍትና ተመሳሳይ ነገሮች በቆሻሻ ክዳን ባላቸው ማጠራቀሚያ ያስወግዱ፣
- በሥራ ቦታ፣ በትራንስፖርትና መኖሪያ ወይም የመኝታ ክፍል መስኮት በመክፈት በቂ አየር እንዲኖር ያድርጉ፣
- መረጃዎችን ከአስተማማኝ ምንጮች ብቻ በመቀበል፣ የተሳሳቱ መረጃዎች የሚያስከትሉትን መደናገርና ፍርኃት ይከላከሉ!
- በሽታውን ሪፖርት ካደረጉ አገሮች የሚመጡ ሰዎች ወይም ንክኪ ያለው ማንኛውም ግለሰብ ራሱን ለ14 ቀን በመለየት በበሽታው አለመያዛቸውን ሲያረጋግጡ ወደ ኅብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ እንመክራለን::
ከኮሮና ቫይረስ እንዴት እንጠበቅ?
- አንድ ሰው ከበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የቅርብ ንክኪ አለው ሲባል በኮሮና ቫይረስ የታመመ ሰው ምልክቱን ማሳየት ከመጀመሩ ሁለት ቀናት በፊት በአንድ ሜትር ርቀት ውስጥ ሆኖ ከአሥራ አምስት ደቂቃ በላይ ቆይታ ሲኖራቸው ነው፡፡
- በተጨማሪም የግል የጤና መከላከያ መሣሪያዎችን ሳይጠቀሙ በበሽታው የተያዘን ሰው እንክብካቤ ሲያደርጉ ነው፡፡ በዚህም መሠረት በበሽታው መታመማቸው ከተረጋገጡ ሰዎች ጋር የቅርብ ንክኪ የነበራቸውን ሰዎች በመለየት በጤና ባለሙያዎች ለ14 ቀናት ክትትል ይደረግላቸዋል፡፡
- በአገራችን ማኅበራዊ ግንኙነታችን፣ የአኗኗር ባህላችን የጠነከረ በመሆኑ በአብዛኛው የምንጠቀማቸው ቁሳዊ ነገሮች በጋራ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ከዚህ አኳያ አንድ በቫይረሱ የታመመ ሰው ነገር ግን መታመሙ በሕክምና እስከሚረጋገጥ ድረስ ከሰዎች ጋር ከሚኖረው ንክኪ በተጨማሪ የሚጠቀምባቸው መገልገያዎች ሌሎችም ሊጠቀሙበት ስለሚችሉ ቫይረሱ በቀላሉ ከሰው ወደ ሰው እንዲተላለፍ ያስችለዋል፡፡
- በሽታው በሳልና በማስነጠስ ወቅትና ከታማሚ ሰው ጋር በሚደረግ የቅርብ ንክኪ፣ ባልታጠበ እጅና በመሳሰሉት ይተላለፋል፡፡
በሽታውን ሪፖርት ወደ አደረጉ አገሮች የሚጓዙ መንገደኞች ሊያደርጓቸው የሚገቡ ጥንቃቄዎች
- የትኩሳትና የሳል ምልክት ከሚያሳዩ ሰዎች ጋር ንክኪ አለማድረግ፣
- እጅን በሳሙናና ውኃ መታጠብ በተለይ ደግሞ ከታመሙ ሰዎች ወይም ከአካባቢያቸው ጋር ንክኪ ካደረጉ፣
- ያልበሰሉ የእንስሳት ተዋጽኦ የሆኑ ምግቦችን ከመመገብ መቆጠብ፣
- ምክንያቱ ባልታወቀ በሽታ በታመሙም ሆነ ከሞቱ የቤትና የዱር እንስሳት ጋር ንክኪ አለማድረግ
በበሽታው መያዛቸውን የጠረጠሩ ሰዎች ማድረግ ያለባቸው ጥንቃቄዎች
- ወደ አገር በተመለሱ በ14 ቀናት ጊዜ ውስጥ የመተንፈሻ አካል ሕመም፣ ትኩሳትና እንደ ሳል ያሉ የሕመም ምልክቶች ካሳዩ፣ በተጨማሪ የበሽታው ስሜት ከመፈጠሩ አሥራ አራት ቀናት በፊት በሽታውን ሪፖርት ወዳደረጉ አገሮች ሄደው ከነበረ፣ በሽታውን ሪፖርት ወዳደረጉ አገሮች ሄዶ የበሽታውን ምልከቶች ማሳየት የጀመረ ሰውን የሚያውቅ ማንኛውም ግለሰብ እንዲሁም የበሽታውን ምልክት ማሳየት የጀመረ ሰውን የሚያውቅ በአስቸኳይ በ8335 ነፃ የስልክ መስመር በመደወል ሪፖርት ያድርጉ፡፡
- በሚያስሉበትና በሚያስነጥሱበት ጊዜ በሽታው ወደ ጤነኛ ሰው እንዳይተላለፍ አፍና አፍንጫን በክንድ ወይም በሶፍት መሽፈን፣
- አፍና አፍንጫን ለመሽፈን የተጠቀምንበትን ሶፍት በአግባቡ በቆሻሻ መጣያ ውስጥ ማስወገድና እጅን ሁል ጊዜ በውኃና በሳሙና መታጠብ ያስፈልጋል፡፡
ኅብረተሰቡ በሽታው በቀላሉ የሚተላለፍ በመሆኑ ሳይዘናጋ የሚተላለፉ መልዕክቶችንና መከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ በማድረግ የበሽታውን ምልክት የሚያሳዩ ሰዎች በሚያገኝበትም ወቅት በተዘረጉ የነፃ የስልክ መስመሮች በመደወል እንዲያሳውቅና የበሽታውን ሥርጭት በመቆጣጠር በኩል የድርሻውን እንዲወጣ አሳስቧል፡፡
ለተጨማሪ መረጃ፣ በነፃ የስልክ መስመር 8335 ወይም በመደበኛ የስልክ ቁጥር 0118276796 ወይም በኢሜይል አድራሻ [email protected] በመጠቀም ማግኘት ይቻላል፡፡
በተጨማሪም ለተለያዩ ጉዳዮች በአንድ ቦታ መሰባሰብን በማስወገድ፣ እጅን አዘውትሮ በመታጠብ፣ ሰዎች በሚሰበሰቡበት ቦታዎች ላይ የአፍንና የአፍንጫ መሸፈኛ (የፊት ማስክ) በማድረግ፣ በአካል ንክኪ የሚደረግ ሰላምታን በመተውና አካላዊ መራራቅን ተግባራዊ በማድረግ የበሽታውን ሥርጭት እንዲከላከል ኢንስቲትዩቱ ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡
የጤና ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት፣ የኮሮና ቫይረስ ሥርጭት መጨመርን ከግንዛቤ በማስገባት ኅብረተሰቡ ጥንቃቄዎችን አዘውትሮ እንዲተገብር አሳስበዋል፡፡ ሁለቱም ተቋማት ዕለት ዕለት በሚደረገው እያንዳንዱ እንቅስቃሴ በበሽታው መያዝን የሚወሰን መሆኑን በማስታወስ፣ የኮሮና ቫይረስ መከላከያ አራቱን የ‹‹መ›› ሕጎች በመተግበር የበሽታውን ሥርጭት ሁሉም እንዲከላከል በጥብቅ አሳስበዋል፡፡
አራቱ የ‹‹መ›› ሕጎች
- መራራቅ፡ አካላዊ ርቀት መጠበቅ፣
- መታጠብ፡ እጅን በተደጋጋሚ በውኃና በሳሙና መታጠብ፣
- መቆየት፡ አስገዳጅ ካልሆነ ቤት ውስጥ መቆየት፣
- መሸፈን፡ ከቤታችን ወጥተን ስንቀሳቀስ የአፍንና የአፍንጫ መሸፈኛ (የፊት ማስክ) መጠቀም፡፡