በተለያዩ ጊዜያት ብሔርን ከብሔር ጋር በማጋጨት ተጠርጥረዋል በተባሉ ሦስት የመገኛ ብዙኃን ላይ ምርመራ መጀመሩን፣ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አስታወቀ፡፡
የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የተደራጁና ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች ዳይሬክተር አቶ ፈቃዱ ፀጋ ለመገናኛ ብዙኃን እንዳስታወቁት፣ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ስቱዲዮ ባላቸው የኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ (ኦኤምኤን)፣ ድምፀ ወያኔ (ዲደብሊዩ) እና አሥራት ሚዲያ ላይ የብርበራ ፈቃድ ከፍርድ ቤት በመውሰድ ምርመራ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡
መገናኛ ብዙኃኑ በዋናነት የተጠረጠሩትና ምርመራ የተጀመረባቸው በተለያዩ ጊዜያት፣ ብሔርን ከብሔር ጋር የሚያጋጩ ዘገባዎችን ማስተላለፋቸውን የሚያመላክቱ ማስረጃዎች በመገኘታቸው መሆኑን ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል፡፡ የምርመራ ሒደቱ የሚከናወነው ቀደም ብለው ያስተላለፏቸው ከነበሩ መረጃዎች ጀምሮ መሆኑንም አክለዋል፡፡
በመገናኛ ብዙኃኑ ስቱዲዮ ውስጥ ምርመራ ከመጀመሩ ባለፈ ስለተገኙ ማስረጃዎች፣ ከጥርጣሬው ጋር ተያይዞ በቁጥጥር ሥር የዋሉ ጋዜጠኞች ስለመኖራቸው፣ መገናኛ ብዙኃኑ የምርመራ ውጤታቸው እስከሚታወቅ ድረስ ሥራ እንዲያቆሙ ስለመደረጋቸው ወይም በሥራ ላይ ስለመሆናቸው ዳይሬክተሩ ያሉት ነገር የለም፡፡
የብሮድካስት ባለሥልጣን ዓርብ ሰኔ 26 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ አሥራት ሚዲያና የኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ቀደም ብሎ ዕርምጃ ተወስዶባቸዋል፡፡ ለትግራይ ቴሌቪዥንና ለድምፀ ወያኔ ቴሌቪዥን ግን የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ መጻፉን አስታውቋል፡፡