የሟቾች ቁጥር እስከ ማክሰኞ 709 ደርሷል
በሁለት ሳምንት ውስጥ ከ256 ሺሕ በላይ ሰዎች ምርመራ ተደርጎላቸዋል
የጤና ሚኒስቴር ነሐሴ 19 ቀን 2012 ዓ.ም. በለቀቀው የኮሮና ወረርሽኝ መረጃ፣ በ24 ሰዓት ውስጥ በተደረገው 18,778 የላቦራቶሪ ምርመራ 1545 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ ተገኝቶባቸዋል፡፡
በኢትዮጵያ ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 43,688 መድረሱን የገለጹት የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር)፣ በዕለቱ የ17 ሰዎች ሕይወት በቫይረሱ ምክንያት ማለፉን ተከትሎ አጠቃላይ የሟቾች ቁጥር 709 መድረሱን ገልጸዋል።
እስከ ነሐሴ 19 ቀን ድረስ ለ794,686 ሰዎች የላቦራቶሪ ምርመራ የተደረገ ሲሆን፣ እስከ ማክሰኞ ቫይረሱ ያለባቸውና ሕክምና እየተከታተሉ የሚገኙት ሰዎች ቁጥር 27,181 ነው፡፡ የጤና ሚኒስቴር መረጃ እንደሚሳየው፣ ከበሽታው ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 15,796 ሲደርስ፣ 290 ሰዎች በፅኑ ሕሙማን ሕክምናቸውን እየተከታተሉ ናቸው።
በተያያዘ ዜና ኮሮና ቫይረስን ለመከላከል በነሐሴ ውስጥ እየተካሄደ ባለው የማኅበረሰብ ንቅናቄና የምርመራ ዘመቻ በ15 ቀናት ከ256 ሺሕ በላይ ሰዎች ምርመራ እንደተደረገላቸው የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።
የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር) ነሐሴ 19 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ እንደገለጹት፣ የተጀመረው የማኅበረሰብ ንቅናቄና የምርመራ ዘመቻ በሁሉም የአገሪቷ ክፍሎች ተጠናክሮ ቀጥሏል።
በዘመቻው “ማስክ ኢትዮጵያ” የተሰኘው የአፍና አፍንጫ መሸፈን መርሐ ግብር መጠናከሩን ገልጸው ክልሎችም በራሳቸው መንገድ እየሠሩበት መሆኑን ጠቁመዋል።
በቀሪዎቹ የነሐሴ ቀናት 270 ሺሕ ሰዎችን ለመመርመር መታቀዱን የገለጹት ሚኒስትሯ፣ኅብረተሰቡ ወቅቱ የወረርሽኝ መሆኑን በመረዳት የሚያደርጋቸውን የጥንቃቄ እርምጃዎች ይበልጥ ሊያጠናክር እንጂ ሊዘናጋ አይገባም ብለዋል።
ሆኖም አሁን አሁን በቤተ እምነቶችና በተለያዩ ሥፍራዎች በብዛት መሰብሰብ እንዳለና አካላዊ ርቀትን መጠበቅ ላይም መዘናጋት መኖሩን ሳይጠቁሙ አላለፉም፡፡
ኅብረተሰቡ ለመጪዎቹ የበዓላት ሰሞን ከወዲሁ ጥንቃቄ እንዲያደርግም ያሳሰቡት ሚኒስትሯ፣ በቫይረሱ ሕይወታቸውን እያጡ ያሉ ሰዎች ሌሎች ተጓዳኝ በሽታዎች የሌሉባቸው መሆናቸውን በመገንዘብ ጥንቃቄው ሊጠናከር ይገባልም ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
ኮቪድ-19 በወረርሽነት ዓለምን ካካለለ ስምንት ወር ሆኖታል፡፡ በእነዚህ ወራት ሕዝበ ዓለም ከኮሮና ቫይረስ እንዲጠበቅ፣ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ እንዳይያዝ የጤና ባለሙያዎችና ዓለም አቀፋዊም ሆነ አገራዊ ተቋማት ማስገንዘቢያዎችን ከመስጠት ችላ ያሉበት ጊዜ አልነበረም፡፡
ኮቪድ-19 የሚተላለፍበት መንገድ አስመልክቶ እስካሁን ያለው አቋም፣ በሽታው ከሕመምተኛው አፍንጫ ወይም አፍ በሚወጣ ጥቂት ፈሳሽ አማካይነት የሚተላለፍ መሆኑ ነው፡፡ ኮቪድ-19 ያለበት ሰው ሲያስነጥስም ሆነ ሲተነፍስ ወደ ሌሎች ከማስተላለፍ ባለፈ፣ ከሕሙማን የሚወጣ ፈሳሽ ያረፈበትን ቦታ የነኩ ሰዎችም በበሽታው በቀላሉ ሊያዙ ይችላሉ፡፡ ሰዎች ከሰዎች ጋር ያላቸው ቅርርብ ከአንድ ሜትር በላይ መሆን አለበት የተባለውም በሽታው በትንፋሽ ስለሚተላለፍ ነው፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ የተደረጉ ጥናቶች የሚያሳዩት ቫይረሱ በአየር ውስጥ ሳይሆን በቫይረሱ ከተያዙ ሰዎች የመተንፈሻ አካላት ከወጡ ፍሳሾች ጋር በሚኖር ንክኪ ብቻ የሚተላለፍ መሆኑን ነው፡፡
ይሁን የቅርብ መረጃዎች የኮሮና ቫይረስ በአየር ላይ የመተላለፍ ዕድሉ ሰፊ መሆኑ እየገለጹ ናቸው፡፡ ይህን ተከትሎ የዓለም ጤና ድርጅት በቫይረሱ የመጋለጥ ወይም ያለመጋለጥ ዙርያ የቀረቡ ጥናቶች ላይ እየመከረ መሆኑ ተዘግቧል፡፡ በአየር ላይ ቫይረሱ በመቆየት ወደ ሌላ ሰው ሊተላለፍ ስለሚችል ተገቢው ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበትም ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡
ተተኳሪ ጉዳዮች
የኖቭል ኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ 19) ከቀላል እስከ ከባድ የመተንፈሻ አካል ሕመም የሚያስከትል የቫይረስ ዝርያ ሲሆን በበሽታው የተያዙ ሰዎች ትኩሳት፣ ሳል፣ የትንፋሽ መቆራረጥና የመተንፈስ ችግር ምልክቶች ይታይባቸዋል፡፡
በዓለም ጤና ድርጅት አገላለጽ፣ ኮሮና ቫይረስ የተለያዩ የቫይረስ ዓይነቶችን የያዘ የቫይረስ ቤተሰብ ነው፡፡ ይህ ቫይረስ በሰዎችና በእንስሳት ላይ በሽታን ያስከትላል፡፡ በሰዎች ላይ የሚከሰተው ኮሮና ቫይረስ የመተንፈሻ አካላትን በመጉዳት ከተራ ጉንፋን እስከ ከፍተኛ የመተንፈሻ አካል ችግር የሚያደርስ ነው፡፡