ኢትዮጵያ ለመጪዎቹ አምስት ዓመታት የልማት ፕሮጀክቶች የምታውለው የ7.1 ቢሊዮን ዶላር የዕርዳታ ስምምነት፣ ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ጋር ተፈራረመች።
ስምምነቱ ጳጉሜን 5 ቀን 2012 ዓ.ም. በገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴና በተመድ የአዲስ አበባ ጽሕፈት ቤት ተጠሪና የተመድ የሰብዓዊ ዕርዳታ የኢትዮጵያ አስተባባሪ ካትሪን ሶዚ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ መፈረሙ ታውቋል።
በስምምነቱ መሠረት የሚገኘው 7.1 ቢሊዮን ዶላር፣ ኢትዮጵያ በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ለምታካሂዳቸው የልማት ፕሮጀክቶች እንደሚውል፣ እነዚህ ፕሮጀክቶች ተመድ በዓለም አቀፍ ደረጃ እ.ኤ.አ. በ2030 እንዲሳኩ ካስቀመጣቸው የዘላቂ ልማት መርሐ ግብር ግቦች ጋር የተጣጣሙ ሆነው የተለዩ ናቸው ተብሏል፡፡
ፕሮጀክቶቹ ከተመድ የዘላቂ ልማት ግቦች ጋር የተጣጣሙ ከመሆናቸው በተጨማሪ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት በቅርቡ ከነደፈው አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የአሥር ዓመታት መርሐ ግብር ጋር ተጣጥሞ የተቀረፀ መሆኑን ከተመድ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሚገኘው ዕርዳታ በዋናነትም በኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ላይ መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች የሚተገበሩበት፣ እንዲሁም የመልካም አስተዳደር፣ የአካባቢና አየር ንብረት ለውጥ ጉዳቶችን ለመቀነስና በሥራ ፈጠራ ላይ ያተኮሩ ኢኮኖሚያዊ ግቦችን በሚያሳኩ ልማቶች ላይ እንደሚውል ከተመድ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የተጠቀሰው የገንዘብ ድጋፍ የመጀመርያ ምዕራፍ መጠን ምንጮች የተለዩ ቢሆንም፣ የተቀረው በሒደት ምንጩ እየተለየ የማሰባሰብ ሥራ እንደሚከናወንና ይህንንም ኃላፊነት በተመድ ሥር የሚገኙ ሁሉም ኤጀንሲዎች እንደሚወጡ ከመረጃው ለማወቅ ተችሏል፡፡
የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ በስምምነቱ ከተፈራረሙ በኋላ ባደረጉት ንግግር፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ለኢትዮጵያ ላሳየው ጠንካራ አጋርነትና ለገባው የድጋፍ ስምምነት መንግሥታቸው ከፍተኛ አድናቆት እንዳለው ገልጸዋል።
ተመድ ከዚህ ቀደም ባደረገው ድጋፍ የኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ገበያ ተኮር እንዲሆን፣ ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች እንዲመሠረቱ፣ እንዲሁም የቴክኒክ ድጋፍ በማድረግ የማይተካ ሚና መጫወቱንና መሠረታዊ የማኅበራዊ አገልግሎቶችን በተለይም ለችግር ተጋላጭ የኅብረተሰበ ክፍሎችን ተደራሽ ሲያደርግ መቆየቱን አስታውሰዋል።
ተመድ ኢትዮጵያ ለምታካሂዳቸው ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ትግበራዎች ከዚህ ቀደም ጠንካራ አስተዋጽኦ ሲያደርግ መቆየቱን በመጥቀስ፣ አሁን የተፈረመው የድጋፍ ስምምነትም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከግብርና መር ወደ ኢንዱስትሪ መር ለማሸጋገር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አስታውቀዋል፡፡