ለ100 ሕሙማን የኩላሊት ንቅለ ተከላ ተደርጓል
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ2012 ዓ.ም. የኩላሊት እጥበት ለሚያስፈልጋቸው 105 ሕሙማን ይሰጥ የነበረውን ነፃ ሕክምና በ2013 ዓ.ም. እንደሚቀጥልም አስታወቀ፡፡
የምሥጋና ቀንን ምክንያት በማድረግ በዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታል የኩላሊት እጥበት እያደረጉ የሚገኙ ሕሙማንን የጎበኙት፣ የከተማዋ ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ ዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታልን ጨምሮ በሦስት የመንግሥት ሆስፒታሎች የኩላሊት እጥበት እያደረጉ ለሚገኙ ሕሙማን አስተዳደሩ 12 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ የ2013 ዓ.ም. ሕክምናቸውን በነፃ እንዲከታተሉ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል፡፡
የኩላሊት እጥበት የሚያስፈልጋቸው ሕሙማን በሳምንት ሦስት ጊዜ በወር 12 ጊዜ የእጥበት ሕክምናውን ማግኘት ያለባቸው ቢሆንም፣ አብዛኞቹ ይህንን ለማድረግ አቅም የላቸውም፡፡ በወር ከ15 ሺሕ ብር በላይ አውጥተው ለመታከም ከባድ በመሆኑም አብዛኞቹ በሳምንት አንዴ ወይም ሁለቴ ብቻ ሕክምናቸውን ሲከታተሉ፣ ይህንን ማድረግ ያልቻሉት ደግሞ ለሕልፈት ተዳርገዋል፡፡
ይህንን ችግር ለመቅረፍ የተቋቋመው የኩላሊት እጥበት በጎ አድራጎት ድርጅት ለቀድሞው የከተማዋ ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) ባቀረበው ጥያቄ መሠረት፣ በድርጅቱ ከታቀፉት 1,400 ሕሙማን መካከል በከፍተኛ ችግር ውስጥ የሚገኙትን 105 ሕሙማን ከ2012 ዓ.ም. ጀምሮ በዘውዲቱ፣ በምኒልክና በጳውሎስ ሆስፒታሎች በነፃ እንዲታከሙ ተደርጓል፡፡
የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን አሰፋ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የተሰጠው ነፃ ሕክምና ዕድል ጳጉሜን 5 ቀን 2012 ዓ.ም. የሚያበቃ የነበረ በመሆኑ፣ ነፃ ሕክምናው እንዲቀጥል ያቀረቡትን ጥያቄ ምክትል ከንቲባ አዳነች ተቀብለው አዎንታዊ ምላሽ በመስጥታቸው አመሥግነዋል፡፡
1,300 ያህል ሕሙማን በከባድ ችግር ውስጥ ሆነው በግል ሆስፒታሎች ሕክምናቸውን እንደሚከታተሉ የገለጹት አቶ ሰለሞን፣ መንግሥት ችግሩን ዓይቶ በመንግሥት ሆስፒታል ያለውን አገልግሎት በማጠናከር ሁሉንም ተጠቃሚ እንዲያደርግና በሆስፒታሎች የሚታየው የግብዓት እጥረት ችግር እንዲፈታ ጠይቀዋል፡፡ በመንግሥት ሆስፒታል የሚከናወን የኩላሊት እጥበት ለአንድ ጊዜ ከእነ መድኃኒቱ 600 ብር ሲሆን፣ በግል ሆስፒታሎች ደግሞ ከ1,300 እስከ 1,600 ብር እንደሆነ የገለጹት አቶ ሰለሞን፣ በግል ሆስፐታል እየከፈሉ የሚታከሙት ወጪው ከአቅማቸው በላይ በመሆኑ ለምግብ ችግር መጋለጣቸውን ጠቁመዋል፡፡
ድርጅቱ ለአንድ ሕመምተኛ በወር ከሚያስፈልገው 8,000 ብር 4,000 ብሩን በመደገፍ 80 ሕሙማንን እየረዳ ሲሆን፣ 22 ደግሞ ከቢጂአይ ኢትዮጵያ በተገኘ ድጋፍ ሕክምናቸውን እየተከታተሉ ይገኛሉ፡፡
ከሁሉም በላይ የኩላሊት ንቅለ ተከላ ሕክምናው ውጤታማ መሆኑን ያስታወሱት አቶ ሰለሞን፣ 100 የድርጅቱ አባላት በጳውሎስ ሆስፒታል ንቅለ ተከላው ተሠርቶላቸው በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል፡፡
ሰው በቁሙ ቃል ገብቶ ሲሞት ኩላሊቱን ንቅለ ተከላ ለሚያስፈልጋቸው እንዲለገስ የኢትዮጵያ የሕግ ማዕቀፍ ስለማይፈቅድ፣ ይህ እንዲሻሻል ከዓመት በፊት እንቅስቃሴ ቢጀምርም ዕውን መሆን አልቻለም ብለዋል፡፡ በቁም ካሉ ዘመድ አዝማድ ኩላሊት ለመቀበል ሕሙማኑ እሺ እንደማይሉ የተናገሩት ሥራ አስኪያጁ፣ መንግሥት ይህንን ችግር ተገንዝቦ የሕግ ማዕቀፉን እንዲያዘጋጅም ጠይቀዋል፡፡