የዋስትና መብት የተከበረላቸው ታሳሪዎች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ ጠየቀ
መስከረም 12 ቀን 2013 ዓ.ም. በ100 ሺሕ ብር ዋስ ከእስር እንዲፈቱ የምሥራቅ ሸዋ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ የሰጠላቸው አቶ ልደቱ አያሌው፣ ማክሰኞ በስቲያ መስከረም 19 ቀን 2013 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ይቀርባሉ፡፡
በኦሮሚያ ክልል የምሥራቅ ሸዋ አዳማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የፈቀደውን ዋስትና ያገደው፣ የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተዘዋዋሪ ችሎት ነው፡፡
ችሎቱ ዕግዱን የጣለው በ100 ሺሕ ብር ዋስ እንዲለቀቁ የተፈቀደላቸው የኢዴፓ አመራር አቶ ልደቱ፣ ከእስር ቢፈቱ ምስክሮችን ሊያባብሉ፣ ሊያስፈራሩና ከአገር ውጭ ከሄዱ ላይመለሱ እንደሚችሉ፣ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ የሥር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በመቃወም ባቀረበው የይግባኝ አቤቱታ ነው፡፡
የቀረበለትን የይግባኝ አቤቱታ የተመለከተው የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተዘዋዋሪ ችሎት፣ ዋስትናውን ለጊዜው አግዶ፣ አቶ ልደቱ ለመስከረም 19 ቀን 2013 ዓ.ም. ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
አቶ ልደቱ ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ መስከረም 12 ቀን 2013 ዓ.ም. በ100 ሺሕ ብር ዋስ ተፈቅዶላቸው፣ ገንዘቡን አስይዘው ከእስር ለመውጣት መፈጸም ያለባቸውን ሥርዓቶች በመፈጸም ላይ እያሉ የሥራ ሰዓት በማብቃቱ፣ በማግሥቱ መስከረም 13 ቀን 2013 ዓ.ም. እንደሚፈቱ እርግጠኛ ሆነው እንደነበር የኢዴፓ ሊቀመንበር ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን በማግሥቱም በተለያዩ ሰበቦች የዋስትና ሒደቱ ዘግይቶ እንዲያድሩ ከተደረጉ በኋላ፣ መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም. ዋስትናው እንደታገደና ቀጠሮ እንደተሰጣቸው አስረድተዋል፡፡
አቶ ልደቱ የፀና ፈቃድ የሌለው የጦር መሣሪያ ይዘው በመገኘት ወንጀል ክስ እንደ ተመሠረተባቸው ይታወሳል፡፡