በአራት ክልሎች እና በሁለት ከተማ አስተዳደሮች የሚገኙና ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች ለሆኑ ሰባት ሚሊዮን ሕፃናት ከመስከረም 27 እስከ 30 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ የፖሊዮ በሽታ መከላከያ ክትባት በዘመቻ እንደሚሰጣቸው የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡
ኢንስቲትዩቱ ለተከታታይ አራት ቀናት የሚቆየውን የክትባቱን ዘመቻ አስመልክቶ መስከረም 22 ቀን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንዳመለከተው ክትባት የሚሰጠው በሶማሌ፣ በኦሮሚያ፣ በሐረሪ፣ በደቡብ ክልሎች፣ እንዲሁም በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች በሚገኙ 47 ዞኖች እና 334 ወረዳዎች ለሚኖሩ ሕፃናት ነው፡፡
ክትባቱ በዘመቻ መልክ ቤት ለቤት በሚደረግ ጉብኝት የሚከናወን ሲሆን ሕፃናቱ ከአሁን በፊት ክትባቱን ቢከተቡም ባይከተቡም አሁን የሚሰጠው የፖሊዮ ክትባት መውሰድ እንደሚኖርባቸው ከመግለጫው ለመረዳት ተችሏል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ በደቡብ ክልል በሚገኙ 11 ወረዳዎችና በአንድ የኦሮሚያ አጎራባች ወረዳ ጨምሮ በአጠቃላይ በ12 ወረዳዎች ለሚኖሩ 704,000 ሰዎች ከጥቅምት 13 ቀን ጀምሮ የቢጫ ወባ መከላከያ ክትባት ለመስጠት የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት በመከናወን መሆኑን አመልክቷል፡፡ ክትባቱን ለመስጠት ያስፈለገው ለወረርሽኙ ሥጋት የሆኑ መንስዔዎች ስለታዩ ነው፡፡
በደቡብ ክልል የካቲት 24 ቀን 2012 በተከሰተው የቢጫ ወባ ወረርሽኝ 86 ሰዎች በሽታ መያዛቸውን እንዲሁም አራት ሰዎች መሞታቸው መግለጫው ጠቁሞ ወረርሽኙን ተከትሎ በተከሰተበት ወረዳ ክትባትን ጨምሮ በተሰጠው ምላሽ ወረርሽኙን ለመቆጣጠር እንደተቻለ አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ የኅብረሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከጤና ሚኒስቴርና ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በአገራችን የተለያዩ ክፍሎች የኅብረተሰብ ጤና ሥጋቶች ላይ የቁጥጥርና ምላሽ ሥራዎችን በመሥራት ላይ እንደሚገኝም ገልጿል፡፡
ፖሊዮ ምንድነው?
ከኅብረተሰብ ጤና ሥጋቶች ውስጥ የፖሊዮ ቫይረስ አንዱ ሲሆን ሕፃናትን ለሕመም፣ ለሞትና ለዘላቂ አካል ጉዳተኝነት የሚዳርግ ከሰው ወደ ሰው የሚተላለፍ በሽታ አምጪ ተህዋስ ነው፡፡ የፖሊዮ በሽታን መከላከል የሚቻለው ሕፃናትን በመደበኛ የክትባት መርሐ ግብርና በዘመቻ መልክ የሚሰጠውን የማጠናከሪያ ክትባት በአግባቡ እንዲከተቡ በማድረግ ነው፡፡
አሁን ባለው ሁኔታ የዋይልድ ፖሊዮ በሽታ በአፍሪካ መጥፋቱ ማረጋገጫ የተሰጠ ሲሆን አገራችን ኢትዮጵያም የመጨረሻውን የዋይልድ ፖሊዮ ቫይረስ በጥር ወር 2006 ዓ.ም. ሪፖርት ባደረገች በሦስተኛው ዓመት ከዋይልድ ፖሊዮ ነፃ መሆኗን በአፍሪካ ደረጃ የተቋቋመ ኮሚቴ የተረጋገጠ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በአጎራባች አገሮች ሲዘዋወር የቆየ በክትባት እጥረት የሚመጣው የፖሊዮ ቫይረስ ለመጀመርያ ጊዜ በግንቦት ወር 2011 ዓ.ም. በሶማሌ ክልል ዶሎ ዞን ቦህ ወረዳ ሲገኝ፣ ተመሳሳይ የሆነ የፖሊዮ ቫይረስ ዝርያም በደቡብና በኦሮሚያ ክልል መገኘቱ ቀደም ሲል መገለጹ ይታወቃል፡፡
ለፖሊዮ ወረርሽኝ መከሰት በዋና ምክንያትነት የሚጠቀሰው የመደበኛ ክትባት አገልግሎት ተደራሽነትና ተጠቃሚነት ዝቅተኛ መሆንና ከፍተኛ የሆነ የክትባት አገልግሎት መጠን ማቋረጥ መኖሩ እንደሆነ የኢንስቲትዩት መግለጫ ያሳያል፡፡