ጉዳዩ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የአውቶማቲክ መክፈያ ማሽን (ATM) ችግሮችን ይመለከታል፡፡ እኔ አቶ እንዳለ ደበበ ገብሬ የተከሰቱትን ችግሮች ሳብራራ መስከረም 5 ቀን 2013 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3፡30 ሰዓት ላይ እንቁላል ፋብሪካ ቅርንጫፍ 1,000 ብር ከማሽኑ ወጪ አድርጌ ወደ መደበኛ ሥራዬ እሄዳለሁ፡፡ ቀኑን ሙሉ ሥራዬን አከናውኜ ከምሽቱ 1.30 ሰዓት ላይ ወደ ቤቴ ስመለስ፣ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ንግድ ባንክ ቅርንጫፍ ጎራ ስል ሁለት የኤቲኤም ማሽኖች ነበሩ፡፡
አንደኛውን ማሽን ክፍያ ስጠይቅ ሊሰጠኝ አልቻለም፡፡ ሁለተኛው ማሽን ግን ከፈለኝ፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ ስልኬ የመጣው መልዕክት ትክክል አይደለም፡፡ ከዚያም ወደ 951 የባንኩ የጥሪ ማዕከል በስልኬ ደወልኩ፡፡ የተሰጠኝ መልስ መስከረም 6 ቀን 2013 ዓ.ም. ጠዋት 3፡00 ሰዓት ላይ ዮሐንስ ቅርንጫፍ ሄደው አነጋግሩ የሚል ነበር፡፡ በወቅቱ እኔም ቅርንጫፉ በመሄድ ኃላፊውን አነጋገርኩ፡፡ ምንም የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ከነገረኝ በኋላ ከኤቲኤም ጋር የሥራ ግንኙነት ያለውን ስታፍ አገናኘኝ፡፡
ከዚያ በኋላ የተሰጠኝ መልስ የእኛ ሲስተም ከፍሎሃል የሚል ነው፡፡ በቦታው ከነበሩት የዮሐንስ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዓብይ ጋር በርካታ መፍትሔ አልባ ንትርክ ካደረግኩ በኋላ፣ በርካታ ቀጠሮዎች ተሰጥተውኝ ተመላልሻለሁ፡፡ በስተመጨረሻ ከአቶ ዓብይ ያገኘሁት ምላሽ ለእኛ አለቃ ለሆነው (ለዲስትሪክት) ማኔጀር ደብዳቤ ስለጻፍን መልሱን ደውለን እንነግራለን ተባልኩ፡፡
ከዚያም የተለያዩ ስልኮች ከባንክ እየተደወሉ ብዙ ጥያቄዎች ይጠይቁኛል፡፡ ማለትም የኤቲኤም ካርድ ቁጥር፡፡ በርካታ ንትርኮች ካስተናገድኩ በኋላ አራት ኪሎ ከሚገኘው የዲስትሪክት ማኔጀር ከአቶ ግርማ ጋር አሰልቺ ውይይት አድርጌ ያለ ምንም ውጤታማ ምላሽ ከ15 ቀናት የምልልስ ሒደት በኋላ ሲስተሙ ክፍያ በትክክል ፈጽሟል የሚል ምላሽ ተቀብዬ ተመለስኩ፡፡ እንግዲህ ይህ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኤቲኤም ችግር በርካታ የአገሪቱን ዜጎች የሚጎዳ ከመሆኑም ባሻገር፣ በየወቅቱ የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታት ምንም የሚወሰዱ ዕርምጃዎች እንደሌሉ ይታየኛል፡፡ ይህ ግዙፍ የሆነ የአገሪቱ የፋይናንስ ተቋም፣ ይህንን ሁሉ ሕዝብ ለማገልገል ራሱን ሪፎርም ለማድረግ የሚደረጉ ክንውኖች ብዙም አይታየኝም፡፡ ይህ ግዙፍ የፋይናንስ ተቋም ራሱን ለማዘመን በርካታ ችግሮች አሉበት፡፡ ስለዚህ ይህንን አገራዊ ተቋም በትኩረትና በአፋጣኝ በሆኑ ተገልጋዩን ለማርካት የሚያደርጋቸው ጥረቶች መንግሥት ጠበቅ ባለ አመራር በርካታ ባለሙያዎችን በቦታው በመመደብ የደንበኞችን ፍላጎት የሚያሟላ መሆን ይገባዋል፡፡
እንግዲህ በእኔ ላይ የደረሰው የሲስተም ብልሹነት ብዙ ወገኖቼ ላይ እያጋጠመ ስለሆነ፣ ወቅቱ የሚጠይቀውን የቴክኖሎጂ ሒደቶች ባንኮቻችን መከተል ካልቻሉ እጅግ ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ ልንገባ እንችላለን፡፡ በተለይ እያንዳንዱ ቅርንጫፍ ባንኮች በየወቅቱ የፋይናንስ ቁጥጥር የማይደረግላቸውና ሕዝብ በአደራ የሰጣቸው ገንዘብ በአግባቡ የማይጠበቅ ከሆነ፣ የሕዝብ አመኔታ የማጣት ችግር ውስጥ ይገባል፡፡
ለማጠቃለል ለበርካታ ችግሮች ትልቁ ቁልፍ መፍትሔ የሚሆነው፣ ሕዝብ በንግድ ባንክ ለሚያጋጥሙት ችግሮች ጥያቄ ሲያቀርብ መፍትሔ የሚገኘው የጋራ ጥረት ሲደረግ ብቻ ይመስለኛል፡፡
(እንዳለ ደበበ ገብሬ፣ ከአዲስ አበባ)