በሔለን ተስፋዬ
የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በኢትዮጵያ ቱሪዝም ላይ ያስከተለውን አሉታዊ ተፅዕኖ በመቅረፍ ዳግም የዘርፉን እንቅስቃሴ ለማስጀመር የተዘጋጀው የጤና አጠባበቅ ፕሮቶኮል መተግበር ጀምሯል፡፡
የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ፕሮቶኮሉን አስመልክቶ ከግል ዘርፍ ባለሀብቶች፣ ከሆቴል ባለቤቶችና ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር መስከረም 21 ቀን 2013 ዓ.ም. ውይይት አካሂዷል፡፡
የቀረበው የፕሮቶኮል ሰነድ በዓለም ቱሪዝም ድርጅት፣ በዓለም ጤና ድርጅትና በአፍሪካ በሽታ መቆጣጠሪያ ማዕከል (ሲዲሲ) መመርያዎችና ከጤና ሚኒስቴር በሚሰጡ ምክረ ሐሳቦች የሚመራና የሚተገበር ነው፡፡
የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ሒሩት ካሳው (ዶ/ር) እንዳሳሰቡት መመርያው በጥብቅ እንዲተገበር በሆቴል ዘርፍ የተሰማሩ ባለሙያዎችና ተቋማት መዘጋጀት አለባቸው፡፡
የቱሪዝም ዘርፉን ወደ እንቅስቃሴ ለማስገባት እየተተገበረ ያለውን ዓለም አቀፍ ፕሮቶኮል ኢትዮጵያም የምትከተለው ይሆናል ያሉት ሚኒስትሯ፣ የቱሪስት ማረፊያና ተቀባዮች የሆኑት ባለሆቴሎችና አስጎብኚ ድርጅቶች ዓለም አቀፍ የጤና አጠባበቅ ፕሮቶኮሉን በትክክል መተግበር እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል፡፡
በኢትዮጵያ የቱሪዝም እንቅስቃሴ ጥቅምት 2013 ዓ.ም. የሚጀመር መሆኑን የገለጹት በሚኒስቴሩ የቱሪስት አገልግሎት ብቃት ማረጋገጥና ደረጃ ምደባ ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ ደርበው፣ ወደ ኢትዮጵያ የሚገባ አንድ ቱሪስት በኮሮና ቫይረስና መሰል ወረርሽኞች ነፃ መሆኑን የሚያሳይ የዓለም አቀፍ የደኅንነትና የንፅህና ማረጋገጫ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
የፕሮቶኮሉ ዓላማ የኅብረተሰቡንና የቱሪስቱን ደኅንነት በመጠበቅ የቱሪስት አገልግሎት አሰጣጡን ማስጀመር ነው፡፡
ፕሮቶኮሉን ተግባራዊ በማድረግ በቱሪዝም ዘርፍ የሚንቀሳቀሱ አካላት ኮሮና ቫይረስን እየተከላከሉ ከወረርሽኙ በኋላ ከሚጎበኙ አገሮች መካከል ኢትዮጵያን አንዷ ለማድረግም ያግዛል፡፡
የንጽሕናና የደኅንነት ፕሮቶኮሉ ከፊል ገጽታ
ፕሮቶኮሉ ለየት የሚያደርገው እንደ ቀድሞው በአንድ መኪና ጎብኚና አስጎብኚ መጓዝ አይችሉም፡፡ አስጎብኚዎችና ምግብ አብሳዮች በተለያየ መኪና መጓዝ እንዳለባቸው ያስገድዳል፡፡ የቱሪስት መስህብ ቦታዎችን ማስጎብኘት ያለባቸው ርቀትን በጠበቀና የፊት ጭምብልን በማድረግ፣ እንዲሁም የሚጎበኘውንም ሥፍራ ዲስኢንፌክት በማስደረግ መሆን አለበት፡፡ ቱሪስቱ ወደሚጎበኘው ቦታ ሲገባ በር ላይ በሚተከለው ማሽን በማሠለፍ ማፅዳት ግዴታ ነው፡፡
የመስተንግዶ አገልግሎትን በተመለከተም ሁሉም የሆቴል ሠራተኞች በጤና ሚኒስቴር በተረጋገጠለት የሕክምና ተቋም የኮቪድ-19 ምርመራ ማድረግና ማረጋገጫ ማግኘት አለባቸው፡፡ የግላቸው የሆነ መልበሻ ክፍል ማዘጋጀት፣ ወደ ሥራ ከመግባታቸው በፊትም ጭምብል ማድረግና በእጃቸው ሳኒታይዘር ይዞ መንቀሳቀስ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህንኑም የሚያረጋግጥ በሆቴሉ የሚመደብ ሰው ክትትል ይደረጋል፡፡
ሌላው አስገዳጅ ነገር ወደ ሆቴሉ የሚገቡ ማንኛውም ዓይነት የምግብ ምርቶች ወደ ሆቴሉ የሚገቡት በተለይ በተዘጋጀ ክፍል ውስጥ ሳኒታይዝ በተደረገ ዕቃ በመቀበል ይሆናል፡፡
ማብሰያ ቤቶችም ርቀታቸውን በጠበቁ አብሳዮች ምግብ እንዲያዘጋጁ ፕሮቶኮሉ ያስገድዳል፡፡ በምግብ አዳራሽም ውስጥ አስተናጋጆች ርቀታቸውን በመጠበቅና ንክኪን በመቀነስ ሥራቸውን ማከናወን ይጠበቅባቸዋል፡፡