በታደለ ደሴ (ዶ/ር)
በዓለም ላይ እስካሁን በርካታ ወረርሽኞች ተከስተው በታሪክ የማይዘነጉ እልቂቶችን ፈጥረው አልፈዋል፡፡ ዕድሜ ለሳይንስ ብዙዎቹ በሕክምና ጠፍተዋል፣ የተቀሩትም ደግሞ አደገኛነታቸው ቀንሶ አሁንም ድረስ አሉ፡፡ ብቅ ጥፍት እያሉ ዓለምን የሚያሸብሩ እንደ ኢቦላ ያሉ አስከፊ ወረርሽኞችም የመዛመት ፍጥነታቸውን ዝቅተኛ ለማድረግም ሳይንስ አልከበደውም፡፡
ከስድስት ወራት በፊት የተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ግን ዓለምን እንደ አንድ መንደር ያደረገ፣ በጂኦግራፊ ሳይገታ የሁሉንም በር ያንኳኳ አስደንጋጭ ክስተት ሆኗል፡፡ ሚሊዮኖችን ለማዳረስ የቀናት ዕድሜ ነበር የፈጀው፡፡ መነሻውን ቻይና ውኃን ከተማ አድርጎ አፍታም ሳይቆይ ወደ ምዕራባውያኑ ተዛመተ፡፡ በሳይንስ በምርምርና ኢኮኖሚ ማማ ላይ የደረሱ አገሮችን ትዝብት ላይ እስኪወድቁ ገመናቸውን አጋለጠ፡፡ የሰው ልጆች ዋነኛ መገለጫ የሆነውን ማኅበራዊ መስተጋብርን መሣሪያው አድርጎ አትጨባበጡ፣ አትውጡ አትግቡ አለ፡፡
ብዙዎች አላመኑም፡፡ ከበስተጀርባው የተለየ አጀንዳ እንዳለ በመገመት ተዘናጉ፣ ወረርሽኙ ፍጥነቱን እየጨመረ መጥቶ በቀናት ውስጥ መቶ ሺዎችን ጉድ አደረገ፡፡ እንዲያም ሆኖ አደብ የገዙ ብዙ አልነበሩም፡፡ 36 ሚሊዮን ሰዎችን ያጠቃል፣ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ዜጎችን ያረግፋል ብሎ የጠበቀ አልነበረም፡፡ ይህ ሁሉ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ሲከሰት በርካቶች ወረርሽኙ አፍሪካ ከገባ አሰቃቂ እልቂት ሊፈጠር እንደሚችል ሲተነብዩ ነበር፡፡
እስካሁን በአፍሪካ 1.4 ሚሊዮን ሰዎች በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ተጠቅተዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ 36,000 ሰው ለኅልፈት የተዳረገ ሲሆን በዓለም ላይ ከተከሰተው ጋር ሲነፃፀር እንደተፈራው ሳይሆን እጅግ ያነሰ ነው፡፡ ከወረርሽኙ የሚያገግመው ሰውም 80 በመቶ መድረሱ እንዴት ነው ነገሩ አስብሏል፡፡ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትም ክስተቱን በሳይንስ አስደግፈው ለመተንተን ሙከራ አድርገዋል፡፡ ለመተንፈሻ አካላት በሽታ ቀድሞ የነበረ ተላማጅነት፣ የአፍሪካ የሕዝብ ስብጥር/የወጣት ኅብረተሰብ ክፍል ብዙ መሆን፣ ፈጣን የበሽታ መከላከል ዕርምጃ በወቅቱ መወሰዱ፣ የእንቅስቃሴ ዕገዳ መጣልና ተፈጥሮአዊ የኦክስጂን አጠቃቀምና ከፍተኛ የፀሐይ ብርሃን መኖር፣ እንዲሁም ከኒያነደርታል የተወረሰ የዘር ቅንጣት በአፍሪካውያን ዘረመል ውስጥ አለመገኘቱ ወረርሽኙ በተፈራው መጠን አፍሪካውያንን እንዳያጠቃ አድርጓል የሚሉ መላምቶች ዋነኞቹ ናቸው፡፡
ያሉትን ብዥታዎች ሊያጠራ የሚችል የምርምር ውጤት ግን በቅርቡ ይፋ ሆኗል፡፡ ግኝቱ እስካሁን ወረርሽኙ የተጠናከረ የጤና መሠረተ ልማት በሌለበት አኅጉር በአፍሪካ ላይ በተፈራው መጠን እልቂት ሳያስከትል ባደጉት አገሮች ላይ ለምን የከፋ ጉዳት ሊያደርስ እንደቻለ ሳይንሳዊ ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡
ምርምሩ ይፋ የተደረገው ባለፈው መስከረም 22 ቀን 2020 ዓ.ም. ኔቸር በተሰኘው ዓለም አቀፍ ታዋቂ የምርምር ውጤቶች በሚታተሙበት መጽሔት ላይ ነው፡፡ በጥናቱ ጥቅም ላይ የዋለው የዘረመል ቅንጣት አደራደር ቴክኒክ በዓለማችን ላይ ትልቅ እመርታ ያመጣና በዘር የሚተላለፉ በሽታዎችን ለመለየት የሚጠቅምና የሳይንስ ዘርፍ ነው፡፡ ጥናቱ ከ3,000 በላይ በሆኑ ሆስፒታል ተኝተው በሚታከሙ ሰዎች ላይ በተወሰደ የዘረ መል ናሙና የተካሄደ ነው (ናሙናው ከአስያ አውሮፓና አፍሪካውያን የተወሰደ ነው)፡፡ ውጤቱም እ.ኤ.አ. በ2020 የተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ከዘር ሐረግ ጋር ያለውን ግንኙነት የሚያሳይ ነው፡፡
በምርምር ግኝቱም የዘረመል ዘንግ (ክሮሞዞም) ሦስት ውስጥ ከሚገኙት ጂኖች ወይም ዘረመል መካከል ውስጥ አንዱ በቀላሉ በኮሮና እንደሚጠቃ ተረጋግጧል፡፡ ይህ ጂን ኒያንደርታል ከተባለው ቀደምት የሰው ዘር የተቀዳ ነው፡፡ ከ50,000 ዓመታት በፊት ዘመናዊው የሰው ዘር ከአፍሪካ ተነስቶ ወደ እስያ ተጉዞ ከመካከለኛው ምሥራቅ ከሚኖረው ኒያንደርታል ጋር ባደረገው ግንኙነት የተፈጠረ መወራረስ ነው፡፡
በጥናቱ ውጤት መሠረት 50 በመቶ የሚሆኑት ደቡብ እስያ፣ 16 በመቶ የሚሆኑ አውሮፓውያን የዚህ ጂን ባለቤት ናቸው፡፡ የኒያንደርታል ጂን በአፍሪካውያን ውስጥ ግን የለም፡፡ በአገር ደረጃ የባንግላዴሽ ሕዝብ 63 በመቶ የሚሆኑት ይህ ጂን በእናት ወይ በአባታቸው አለባቸው፡፡ በእንግሊዝ ውስጥ በተደረገው በዚሁ ጥናት ውጤት መሠረት በኮቪድ-19 ከሞቱ ሰዎች መካከል የባንግላዴሽ ዝርያ ያለባቸው ታማሚዎች ከአጠቃላይ ታማሚዎች ከእጥፍ በላይ ሞተዋል፡፡ በአንጻሩ የአፍሪካ ዝርያ ያላቸው ታማሚዎች ግን ይህ ጂን ስለሌለባቸው ጉዳታቸው የከፋ ሳይሆን ቀርቷል፡፡
እንደተጠቀሱት የደቡብ እስያና የአውሮፓ አገሮች ሁሉ በደቡብ አፍሪካ ውስጥ ከፍተኛ የኮቪድ-19 ጉዳት መከሰቱ የሚያያዘው አብዛኛው የደቡብ አፍሪካ ታማሚዎች የዘር ሐረጋቸው ከአውሮፓ የሚመዘዝ በመሆኑና ተጠቂ የሚደርጋቸውን የዘረመል ቅንጣት የወረሱ በመሆናቸው ነው፡፡ በሽታው የኒያንደርታል ጂን ባለባቸው ሰዎች ላይ እንደሚበረታ የሚያሳየው ጥናቱ፣ አፍሪካውያን ከጂኑ ነፃ በመሆናቸው ዱላው አልበረታባቸውም ሲል ይደመድማል፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡