በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተደጋጋሚ እየደረሰ ካለው ጥቃት ጀርባ ያለው ዋነው ዓላማ፣ ወደ ታላቁ የህዳሴ ግድብ የሚወስደውን መንገድ መቆጣጠር እንደሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን የተናገሩት ጥቅምት 9 ቀን 2013 ዓ.ም. የመንግሥታቸውን ዓመታዊ ዓበይት ተግባራት በተመለከተ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኝተው ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው።
በወቅቱ የምክር ቤቱ ከባላት ካነሱላቸው ጥያቄዎች አንዱ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በነዋሪዎች ላይ በተደጋጋሚ እያጋጠመ ያለውን ጥቃት የሚመለከት ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ምላሽም በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የብሔር ችግር እንዳለ ለማስመሰል ቢሞከርም፣ ነገሩ ግን ከዚያ በላይ የተወሳሰበ እንደሆነ ገልጸዋል።
በአካባቢው በተደጋጋሚ በዜጎች ላይ እየተከፈተ ያለው ጥቃት በውጭና በውስጥ ኃይሎች ቅንጅት የሚፈጸም እንደሆነ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር)፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የተጎነጎነው ሴራ ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጋር እንደሚገናኝ ጠቁመዋል።
‹‹በአካባቢው ለመፍጠር እየተሞከረ ያለው ከህዳሴ ግድቡ ጋር ይገናኛል። ዓላማውም ወደ ህዳሴ የሚወስደውን መንገድ ከመቁረጥ ጋር ይያያዛል፤›› ብለዋል።
ጥቃቱ የሚሰነዘርበት አካባቢ ከጎረቤት አገር ጋር የሚያዋስን ሰፊ ድንበር የሚሸፍን በመሆኑና በአካባቢው ምንም ዓይነት መንገድ ባለመኖሩ፣ የመከላከል ሥራውን ፈታኝ እንዳደረገው ገልጸዋል።
ጥቃቱ በሚያጋጥምባቸው ሥፍራዎች የመኪና መንገድ ባለመኖሩ፣ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ጥቃት የተፈጸመበት ቦታ ለመድረስ እስከ 7፡00 ሰዓት ድረስ በረዣዥም ሳር ውስጥ በእግራቸው እንደሚጓዙ አስረድተዋል።
‹‹ጥቃቱ የሚፈጸመው በቀስት ነው። የመከላከያ ሠራዊቱ በረዣዥም ሳር (ሳቫና ግራስ ላንድ) ውስጥ ጥቃት አድራሾችን ለመያዝ በሚያደርጉት እንቅስቃሴ፣ ብዙ መስዋዕትነት ከፍለዋል፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በዚህ መስዋዕትነትም በመቶ የሚቆጠሩ ሰዎች መማረካቸውንና ብዙዎቹ ጥቃት አድራሾች ደግሞ መሸሻቸውን ተናግረዋል።
አጥቂዎቹ መሠረታቸውን ያደረጉት በግድቡ አቅራቢያ በምትገኝ ‹‹ብሉ ናይል›› በተባለች የሱዳን ግዛት ውስጥ እንደሆነና በዚያም በስም ባልጠቀሷቸው የውስጥና የውጭ አካላት ሥልጠናና ሌሎች ድጋፎችን ወስደው በንጹሐን ላይ ጥቃት እንደሚከፍቱ ተናግረዋል።
‹‹ችግሩ አሁንም ከምንጩ ካልደረቀ ዳግም ችግር ይከሰታል›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መንግሥታቸው ለችግሩ ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት እየሠራ መሆኑን አመልክተዋል።
ምንም ዓይነት እክል ቢመጣ ሉዓላዊነትን ለማስከበር በሕይወት መስዋዕት እስከመሆን ዋጋ እየከፈለ በሚገኘው መከላከያ ሠራዊት አማካይነት ችግሮቹን ለማስወገድ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
ምንም ዓይነት ችግር ቢከሰት እንኳን ይህ መንግሥት ባለው አቅም ከህዳሴው ግድብ ላይ ዓይኑን ሳያነሳ ዕውን እንደሚያደርገው የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የህዳሴ ግድቡ ቁልፍ ሥራ ዘንድሮ በመሆኑ እንደ አገር በጋራ መቆም እንደሚገባ አሳስበዋል።
‹‹ፀሐይም ሆነ ዝናብ ሲመጣ ከመንገዳችን መቆም ሳይሆን ጥላ ይዘን ጉዟችንን እንቀጥላለን” በማለት የህዳሴው ግድብ ግንባታ በማንኛውም እክል ምክንያት ሊገታ እንደማይችል በአጽንኦት ገልጸዋል።