የወጋገን ባንክ ፕሬዚዳንት በመሆን ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ዓባይ መሐሪ፣ ከኃላፊነታቸው ለመልቀቅ ያቀረቡትን ጥያቄ የባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ ተቀብሎ አሰናበታቸው፡፡ እሳቸውን ተክተው እንዲሠሩ አዲስ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሰይሟል፡፡
ምንጮች እንደገለጹት አቶ ዓባይ ከኃላፊነታቸው ለመልቀቅ በተደጋጋሚ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ የባንኩ ቦርድ ጥያቄያቸውን የተቀበለው ከወራት ቆይታ በኋላ ባለፈው ሳምንት ሲሆን፣ የስንብት ጥያቄያቸው አዎንታዊ መልስ በመስጠት ከኃላፊነታቸው መልቀቃቸው ተረጋግጧል፡፡
አቶ ዓባይ ከኃላፊነታቸው ለመልቀቅ ምክንያት የሆናቸው ጉዳይ ባይታወቅም፣ የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ አግባብቷቸው ኃላፊነታቸውን ይዘው ለተወሰኑ ጊዜያት እንዲቆዩ ማድረጉን ምንጮች ገልጸዋል፡፡
አቶ ዓባይ የወጋገን ባንክ ፕሬዚዳንት ሆነው ከመሾማቸው ቀደም ብሎ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በምክትል ፕሬዚዳንትነት ከማገልገላቸው በተጨማሪ፣ በባንክ ኢንዱስትሪ ውስጥ ለረዥም ዓመታት ቆይተዋል፡፡ ወጋገን ባንክን አምስተኛው ፕሬዚዳንት ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ዓባይ፣ ባንኩን የተቀላቀሉት በየካቲት 2012 ዓ.ም. እንደነበር ይታወሳል፡፡
የወጋገን ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ በአቶ ዓባይ ምትክ የእናት ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ብርቱካን ገብረ እግዚን በተጠባባቂነት ሰይሟል፡፡
ወ/ሮ ብርቱካን በባንክ ኢንዱስትሪው ውስጥ ከ30 ዓመታት በላይ ያገለገሉ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ20 ዓመታት በላይ ሠርተዋል፡፡ በንግድ ባንክ ቆይታቸው እስከ ከፍተኛ የማኔጅመንት አባልነትና በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ የሠሩ፣ የእናት ባንክ እንዲመሠረትና ሴቶች የኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ መሆን እንደችሉ ብርቱ ጥረት በማድረግ የሚታወቁ ሲሆን፣ በአቢሲኒያ ባንክም በተመሳሳይ ከሦስት ዓመታት በላይ አገልግለዋል፡፡ ላለፉት ስምንት ዓመታትም የእናት ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት በመሆን ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡