በሲሳይ ሳህሉ
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሚገኙ ከ200,000 በላይ ባለቤት አልባ ውሾች ለነዋሪዎች ሥጋት መሆናቸውን፣ በከተማ አስተዳደሩ የአርሶ አደርና ግብርና ልማት ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
በኅብረተሰቡ ዘንድ ውሻን ያለመንከባከብና ተገቢውን ክትትል ያለማድረግ ባህል ጋር ተዳምሮ፣ ባለቤት የሌላቸውን ውሾች ለመከተብና አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ እንዲገደሉ ለማድረግ የሚያስችሉ መድኃኒቶች በበቂ ሁኔታ አለመኖር፣ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች በርከት ያሉ ውሾችን ማየት ለኅብረተሰቡ ጤና አሳሳቢ መሆኑን የተቋሙ የእንስሳት ጤና ዳይሬክተር ፋሲካ በለጠ (ዶ/ር) ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
እንደ ዳይሬክተሯ ገለጻ ምንም እንኳ ሁሉን አቀፍ በሆነ ጥናት የተደገፈ መረጃ ባይኖርም፣ በከተማ አስተዳደሩ ከ90,000 በላይ ባለቤት ያላቸውና ከ210,000 በላይ ባለቤት አልባ ውሾች ይኖራሉ፡፡
የክትባት መድኃኒቶቹን ቢሾፍቱ (ደብረ ዘይት) ከሚገኘው የእንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት የሚያገኘው ተቋሙ፣ ዘንድሮ ከ23,000 በላይ ባለቤት ያላቸውንና ወደ 45,000 የሚጠጉ ባለቤት አልባ ውሾችን ለመከተብ ያቀደ ቢሆንም፣ የመድኃኒት አቅርቦቱ በተገቢው መጠን አለመቅረቡ ለተቋሙ ከፍተኛ ሥጋት መሆኑን ዳይሬክተሯ አክለዋል፡፡
‹‹የባለቤት አልባ ውሾች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ አሳሳቢነት እንደ ተቋም ሥጋት ቢሆንብንም፣ ሥራው በአንድ ተቋም ብቻ የማይሠራ በመሆኑና ሌሎች አካላት ለጉዳዩ ያላቸው ትኩረት ዝቅተኛ መሆን ከኅብረተሰቡ የግንዛቤ ማነስ ጋር ተዳምሮ ችግሩን የከፋ ያደርገዋል፤›› ብለዋል፡፡
ከዚህም ጋር ተያይዞ የከተማው ነዋሪዎች ውሾችን የመንከባከብና የባለቤትነት ሠርተፊኬት መያዝ እንዳለባቸው የጠቆሙት ዳይሬክተሯ፣ ገና ከመነሻው ከቤት አውጥተው ካልጣሉዋቸው ባለቤት አልባ ሊሆኑ እንደማይችሉ ገልጸዋል፡፡
ተቋሙ ባለፈው ዓመት ከ13,000 በላይ ውሾችን እንዲከተቡ ያደረገ ቢሆንም፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣው የባለቤት አልባ ውሾች ቁጥር በዚህ ከቀጠለ ኅብረተሰቡ ለዕብድ ውሻ በሽታ የመጋለጥ ዕድሉ የበለጠ እየሰፋ እንደሚሄድ ዳይሬክተሯ አስታውቀዋል፡፡