አሜሪካውያን ዴሞክራቱን ጆሴፍ ሮቤንቲ ባይደንን የአሜሪካ 46ኛ ፕሬዚዳንት አድርገው መርጠዋል፡፡ ለአንድ ወሰነ ፕሬዚዳንት ያገለገሉት ዶናልድ ጆን ትራምፕ፣ አሜሪካ ያላትን ሥርዓት አፋልሰዋል ብለው የሚምኑት ተመራጩ ፕሬዚዳንት ባይደን ‹‹ወቅቱ አሜሪካ የምትፈወስበት›› ነው ብለዋል፡፡
በዚህ ወር ማብቂያ 78ኛ ዓመታቸውን የሚያከብሩት የቀድሞ ምክትል ፕሬዚዳንትና የአሁኑ ተመራጭ ፕሬዚዳንት ባይደን በዓለ ሲመታቸው ሲከናወን ከፊታቸው የሚጠብቃቸው በርካታ ሥራዎች እንደሆኑ ሲኤንኤን አስፍሯል፡፡
አሜሪካ ባለፉት 100 ዓመታት ያልገጠማትን ዓይነት የጤና ቀውስ ገጥሟታል፡፡ እ.ኤ.አ. ከ1930 በኋላ ያልታየ የኢኮኖሚ ውድቀት እንዲሁም ዘረኝነትና የፖሊስ አረመኔነት በአሜሪካ ታይቷል፡፡ ይህ በዋናነትና ሌሎችም ባይደንን የሚጠብቁ የቤት ሥራዎች ናቸው፡፡
የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ያሉትም ይህንኑ ነው፡፡ ‹‹ባይደን ጥር ላይ ዋይት ሐውስ ሲገባ ከዚህ ቀደም መሪዎች ያልገጠማቸው ችግሮች ይገጥሙታል፡፡ የኮቪድ -19 ወረርሽኝ፣ ፍትሐዊ ያልሆነ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትና የፍትሕ ዕጦት፣ አደጋ ውስጥ የወደቀ ዴሞክራሲና የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔ የሚፈልጉ ናቸው፡፡ ሆኖም የሁሉንም አሜሪካውያን የመረጡትንም ያልመረጡትንም ፍላጎት ለማሟላት እንደሚሠራ አውቃለሁ፡፡››
የምርጫ ውጤቱ አሜሪካ ክፉኛ እንደተከፋፈለች ያሳያል ያሉት ኦባማ፣ ይህንን ባይደንና ምክትላቸው ካሜላ ሃሪስ ብቻ የሚወጡት ባለመሆኑ ሁሉም አሜሪካውያን የድርሻቸውን መሥራት ይገባቸዋልም ብለዋል፡፡
ተመራጩ ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ምን አሉ?
ዕጩ ተወዳዳሪዎች በምረጡኝ ዘመቻ ወቅት ሊያደርጉ የማይችሏቸውን ሁሉ ቃል ይገባሉ፡፡ ሆኖም ባይደን የፕሬዚዳንትነት በዓለ ሲመታቸውን ሲፈጽሙ በምረጡኝ ቅስቀሳ ወቅት የገቧቸውን ቃሎች ‹ይደግሟቸዋል› ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የኮቪድ-19 መተግበሪያ ዕቅድ
ባይደን ቢሮ የሚይዙት ቫይረሱ ከ230 ሺሕ በላይ አሜሪካውያንን ከገደለ በኋላ ነው፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ትራምፕ በሰጧቸው እርስ በርስ የተጣረሱ መረጃዎች ሕዝቡ ግራ ተጋብቷል፡፡ ባይደን ይህንን ብዥታ ለማፅዳት ምርጫ ከመካሄዱ አንድ ቀን አስቀድሞ ባደረጉት የምረጡኝ መዝጊያ ንግግር ቫይረሱን ለመዋጋት ዕቅድ ማድረጋቸውን አሳውቀዋል፡፡ ተመራጭ ፕሬዚዳንት ሲሆኑም፣ 12 አባላት ያሉት የኮቪድ-19 ግብረ ኃይል አቋቁመዋል፡፡ ከተመረጡበት ከመጀመርያ ቀን አንስቶ ቫይረሱን ለመቆጣጠር ለወራት ሲናገሯቸው የነበሩትን አፍና አፍንጫ መሸፈን፣ ርቀትን መጠበቅ፣ መመርመርና ንክኪ ያለባቸውን ለመድረስ፣ ክትባት ከተገኘ በነፃ ለሁሉም ማዳረስ ማድረግ እንደሚፈልጉ አስታውቀዋል፡፡
የአየር ንብረት ለውጥ
የንፁህ ኃይል አጠቃቀምን ለማቅናት ልዩ ትዕዛዝ እንደሚያስተላልፉ ቃል የገቡት ባይደን፣ ባራክ ኦባማ የፈረሙትና በትራምፕ ዘመን ከታገደው የፓሪስ የአየር ንብረት ጥበቃ ስምምነት አሜሪካን መልሶ ማስገባትም ዕቅዳቸው ነው፡፡
የአሜሪካ ሕንፃዎች፣ ውኃ፣ ትራንስፖርትና የኃይል መሠረተ ልማት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖዎችን የሚመክት እንዲሆን ‹‹ስማርት ኢንቨስትመንት›› ለመተግበርም አልመዋል፡፡
የስደተኞች አቀባበል
የትራምፕ ዘመን ከተወቀሰበት ከዋነኞቹ የሚመደበው የስደተኞችን አጀንዳ መሰባበሩ ነው፡፡ ትራምፕ ለስደተኞች ቦታ የላቸውም፡፡ ባይደን በትራምፕ ዘመን የተወሰኑና ቅሬታ ያስነሱ ጉዳዮችን ይቀለብሳሉ ተብሏል፡፡ የኢሚግሬሽን ሕግ እንደሚኖርም ተናግረዋል፡፡ በአሜሪካ ያለ ሕጋዊ ወረቀት ለሚኖሩ 11 ሚሊዮን ስደተኞች ዜግነት የሚያገኙበትን ሰነድ ለኮንግረሱ ማቅረብም የመጀመርያ ቀን ሥራቸው ነው፡፡ ትራምፕ ከሙስሊም አገሮች ስደተኞች እንዳይገቡ ብለው ያስቀመጡት ገደብም እንዲነሳ ያደርጋሉ ተብሏል፡፡
ውጭ ግንኙነት
ትራምፕ ሰሜን ኮሪያን ወደ ሰላም ለማምጣትና እስራኤልና መካከለኛው ምሥራቅን ለማቀራረብ መጣራቸው ከሠሯቸው ሥራዎች በበጎነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ሆኖም ከቻይና፣ ከሜክሲኮ፣ ከአፍሪካና ከሌሎች አገሮች ጋር ያላቸውን ግንኙነት አበላሽተዋል፡፡ ባይደን የተበላሹ የውጭ ግንኙነቶችን ለማደስ እንደሚሠሩ አስታውቀዋል፡፡
ሹመቶችን አካታች ማድረግ
ከሜላ ሃሪስ የመጀመርያዋ የአሜሪካ ተመራጭ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነዋል፡፡ የባይደን ዘመቻም ቃል የገባው በዋይት ሐውስ ቁልፍ ቦታዎች ውስጥ ሴቶችን ማምጣት ነው፡፡ የተለያየ ቀለም ያላቸውን ሰዎች በመንግሥት ሥራና በካቢኔያቸው ማካተትም ቃል ከገቧቸው አጀንዳዎች መካከል ይጠቀሳል፡፡
ባይደን አሜሪካ ተመልሳ የዓለም ጤና ድርጅትን የምትቀላቀልበትን፣ ፍትሕን ማስፈንና የዘር አድልኦን ማስቀረትን የሚሠሩበት ጉዳይ እንደሆነም አስታውቀዋል፡፡