ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ደመቀ መኮንን ዘሬ ህዳር 7 ቀን 2013 ዓም በኡጋንዳ ተገኝተው በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ዙሪያ ከፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ጋር መምከራቸው ተሰማ።
ኡጋንዳ በፌደራልና በትግራይ ያለውን ጦርነት በውይይት ለመፍታት እንዲቻል የፌዴሬል መንግስት አመራሮችንና የህወሓት አመራሮችን ልታደራድር እንደሆነ የተለያዩ መረጃዎች ከትላንት ምሽት ጀምሮ ሲያሰራጩ እንደነበር ይታወሳል።
ይህንንም ተከትሎ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የሚያስፈጽመው ግብረ ሃይል መረጃው የተሳሳተ እንደሆነና የፌዴራል መንግስት በትግራይ ክልል ለጀመረው የህግ ማስከበር እርመጃ ቁርጠኛ መሆኑን ዛሬ ጠዋት አስታውቋል።
ይህ ቢሆንም ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ደመቀ መኮንን ዛሬ በኡጋንዳ ተገኝተው ከፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ጋር መወያየታቸውን ፕሬዝዳንቱ በቲውተር ገጻቸው ይፋ አድርገዋል።
ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ከአቶ ደመቀ ጋር በትግራይ ክልል ያለውን ግጭት በሚመለከት መወያየታቸውንና መምከራቸውን ገልጸው ፤ ” በኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖር ጦርነት ለአፍሪካ አህጉር መጥፎ ገጽታ የሚፈጥር ነው” ብለዋል።
በአፍሪካ የፖለቲካ ርዕዮተዓለም ላይ ያሉ ልዩነቶችን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ በውይይት የመፍታት ትልቅ ችግር መኖሩን የገለጹት ፕሬዝዳንቱ ፤ ” እኔ ብሔርን መሠረት ያደረገ የፌዴራሊዝም ፖለቲካን ሙሉ በሙሉ አልስማማበትም” ብለዋል።
ፕሬዚዳንቱ ይህንን ያሉበትን ምክንያት ግን አልገለጹም።