ሕይወታቸው ያለፈው ከ1500 በላይ ሆኗል
ከዓምና መጋቢት ወር ጀምሮ በተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ታማሚ የሆኑ ሰዎች ቁጥር ከ100 ሺ በላይ በማሻቀቡ ኢትዮጵያን ከምሥራቅ አፍሪካ ክፍለ አኅጉር ቀዳሚ አድርጓታል፡፡
የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጠየና ኢንስቲትዩት እንዳስታወቀው፣ እስከ ኅዳር 7 ቀን ድረስ ለ1,566,221 ሰዎች የላቦራቶሪ ምርመራ ተደርጎላቸው 103,056 ሰዎች በበሽታው እንደተያዙ፣ ሌሎች 64,130 ሰዎች እንዳገገሙ፣ 37,343 ሰዎችም ቫይረሱ እንዳለባቸውና 1,581 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል፡፡
ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች አገሮች የኮቪድ-19 ሥርጭት ለመከላከል ከወሰዷቸው የመከላከል ዕርምጃዎች በዋናነት የእንቅስቃሴ ገደብ መጣል፣ ትምህርት ቤቶችን መዝጋት፣ የአደባባይ ላይ መሰባሰቦችን ማቆምና ስፖርታዊ ውድድሮችን በጊዜያዊነት ማቋረጥ እንደነበረ ነው ያመለከተው፡፡
የኮቪድ-19 በወጣቶች የኑሮ ዘይቤ ላይ ተፅዕኖ መፍጠሩን፣ በተለይም በአገራችን የትምህርት ቤቶች መዘጋት ብሎም ወጣቶች ተሰባስበው ከሚያደርጉት የማስ ስፖርት እንቅስቃሴ እንዲቆጠብ መደረጉን ከኢንስቲትዩቱ ማብራሪያ ለመረዳት ተችሏል፡፡
ይህን ተከትሎ የጤና ሚኒስቴርና ኢንስቲትዩት ከተለመደው የኑሮ ዘይቤ መራቁና በአንድ ቦታ ለረዥም ጊዜ መቆየቱ ለጭንቀትና ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች ሊያጋልጡ ስለሚችሉ የኮቪድ-19 ወረርሽኝን እየተከላከሉ በመኖሪያ አካባቢያቸው ወይም በቤት ውስጥ አካላዊ ርቀታቸውን ጠብቀው እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ መልዕክት አስተላልፏል፡፡
በዚህም መመርያ መሠረት ትምህርት ቤቶች እንዲከፈቱ፣ የመከላከያ መንገዶችን በመጠቀም ባሉበት ሆነው የስፖርታዊ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉና ሌሎች ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተግባራቶችን እያከናወኑ እንደሚገኙ ኢንስቲትዩቱ ሳይገልጽ አላለፉም፡፡
በተቃራኒው ግን የኮቪድ-19 ሥርጭት እየጨመረ ባለበት በዚህ ሰዓት አንዳንድ ወጣቶች ኃላፊነት በጎደለው መልኩ አካላዊ ርቀትን ሳይጠብቁ ተሰብስበው ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ፣ በመዝናኛ ቦታና በሚንቀሳቀሱበት ወቅት የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ሳያደርጉ ሲንቀሳቀሱ እንደሚስተዋሉ ነው ያመለከተው፡፡