የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን የጋራ መኖሪያ ቤቶችን የውስጥ ለውስጥ መንገዶች በ4.5 ቢሊዮን ብር ሊያስገነባ መሆኑን አስታወቀ፡፡
ከ118 ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ያላቸውን የውስጥ ለውስጥ መንገዶች ፕሮጀክት ለማከናወን ባለሥልጣኑ ከኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሸን ጋር ሐሙስ ኅዳር 10 ቀን 2013 ዓ.ም. የተፈራረመ ሲሆን፣ ሥራውም በአማካይ እስከ 19 ወራት ይፈጃል ተብሏል፡፡
ከ11 እስከ 38.9 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያላቸው የመንገድ ፕሮጀክቶቹ በቦሌ አራብሳ፣ በየካ ጣፎ፣ በጀሞ ጋራ፣ በኮዬ ፈጬና በጨፌ ኮንዶሚኒየም ቤቶች አካባቢ እንደሚገነቡ ተገልጿል፡፡
የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሞገስ ጥበቡ (ኢንጂነር) ከኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዮናስ አያሌው (ኢንጂነር) ጋር ስምምነቱን ሲፈራረሙ እንደተገለጸው፣ ግንባታቸውን ለማካሄድ የኮንትራት ውል ከተገባላቸው ስምንት የመንገድ ፕሮጀክቶች ውስጥ 50 ኪሎ ሜትር ያህሉ በአስፋልት ኮንክሪት የሚሠራ ነው፡፡ እንዲሁም 68.4 ኪሎ ሜትር ደግሞ የኮብልስቶን ንጣፍ ይለብሳል፡፡
በፕሮጀክቱ የተያዙት የጋራ መኖሪያ ቤቶች የውስጥ ለውስጥ መንገዶች በታቀደላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ፣ ባለሥልጣኑ ቁጥጥር እንደሚያደርግም ተጠቁሟል፡፡
በተያያዘ ዜና የቦሌ ሚካኤል አደባባይ ላይና ታች-ቡልቡላ-ካባ መግቢያ የመንገድ ግንባታ ዋና ዋና መጋጠሚያዎች ላይ የተጀመረውና ከወሰን ማስከበር ነፃ የሆነው የመንገድ ክፍል፣ የመጀመርያ ደረጃ አስፋልት የማንጠፍ ሥራ መጠናቀቁ ተገልጿል፡፡
ለትራፊክ እንቅስቃሴ አስቸጋሪ የሆኑ ዋና ዋና፣ የቀለበት የውስጥ ለውስጥና አቋራጭ መንገዶችን የጉዳት መጠን በመለየት የጥገና ሥራ በማከናወን ላይ የሚገኘው ባለሥልጣኑ፣ ባለፉት አራት ወራት 225 ኪሎ ሜትር የመንገድ ጥገና ማድረጉን አስታውቋል፡፡
ባለሥልጣኑ ካከናወናቸው 13 ኪሎ ሜትር የአስፋልት፣ 220 ኪሎ ሜትር የፍሳሽ መስመሮች ፅዳትና ጥገና፣ የዘጠኝ ኪሎ ሜትር ጠጠር መንገድ፣ የሦስት ኪሎ ሜትር የእግረኛ መንገድና የከርቭ ስቶን ጥገና ማከናወኑንም ገልጿል፡፡
ባለሥልጣኑ በ2013 በጀት ዓመት ከ525 ኪሎ ሜትር በላይ የተበላሹ አስፋልት መንገዶችንና ተጨማሪ የመንገድ ጥገና የሚቀናውን ዕቅድ መያዙ አይዘነጋም፡፡