ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን አደጋ ላይ ለመጣልና የተንኮል ድርጊቶችን ግዙፍ በሆነ ዓይነት ማሰናዳት የሚሉ ድንጋጌዎችን መተላለፍ የሚል የወንጀል ሕግ ተጠቅሶ የወንጀል ክስ የቀረበባቸው አቶ ልደቱ አያሌው፣ የቀረበባቸው ክስ ግልጽነት ስለሚጎድለው እንዲሻሻል ፍርድ ቤት ኅዳር 11 ቀን 2013 ዓ.ም. ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
በኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የምሥራቅ ሸዋ ዞን ተዘዋዋሪ ችሎት ዓርብ ኅዳር 11 ቀን 2013 ዓ.ም. በአቶ ልደቱ ላይ የቀረበውን ክስና ክርክሮች መርምሮ በዋስትናና ጠበቆቻቸው ባቀረቧቸው ሌሎች የመብት ጥያቄዎች ላይ ብይን እንደሚሰጥ የተጠበቀ ሲሆን፣ የኦሮሚያ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 238 እና 256 ድንጋጌዎችን ጠቅሶ ያቀረበው ክስ ግልጽነት እንደሚጎድለውና ውሳኔ ለመስጠትም ስለሚያዳግተው ብይን መስጠት እንዳልቻለ መግለጹን፣ የኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ አዳነ ታደለ ለሪፖተር ተናግረዋል፡፡
በመሆኑም በቀረቡለት የመብት ጥያቄዎች ላይ ውሳኔ ለመስጠት ክሱ መሻሻል እንዳለበት ገልጾ፣ ዓቃቤ ሕግ ክሱን አሻሽሎ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ መስጠቱን አክለዋል፡፡
የዋስትና ጥያቄ ለመፍቀድ ወይም ለመከልከል ተሻሽሎ የሚቀርበው ክስ የግድ መታየት እንዳለበት በማሳወቅ፣ ክሱ ለኅዳር 24 ቀን 2013 ዓም. ተሻሽሎ እንዲቀርብ ትዕዛዝ መስጠቱን አቶ አዳነ ገልጸዋል፡፡
አቶ ልደቱ ‹‹የሽግግር መንግሥት ማቋቋም›› እና ‹‹ከድጡ ወደ ማጡ›› የሚሉ መጣጥፎችን በማዘጋጀት ሕዝብን ለአመፅ ለማነሳሳት፣ ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን አደጋ ላይ ለመጣል መዘጋጀት ወንጀል ክስ እንደ ቀረበባቸው መዘገቡ ይታወሳል፡፡