Sunday, June 4, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናአብን ሥልታዊ የዘር ማፅዳትና ማጥፋት እንቅስቃሴዎች እየታዩ ነው አለ

አብን ሥልታዊ የዘር ማፅዳትና ማጥፋት እንቅስቃሴዎች እየታዩ ነው አለ

ቀን:

የአማራና የአገው ሕዝብ ሲፈጸሙበት ከቆዩት ሰፊ ዘር ተኮር ጥቃቶች ሳያገግም፣ በኦሮሚያና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች ውስጥ፣ በአማራ ጠልነት መንፈስ ሥልታዊ የዘር ማፅዳትና ማጥፋት እንቅስቃሴዎች እንደ አዲስ ተጠናክረው እየታዩ መሆኑን መገንዘቡን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አስታወቀ፡፡

ማክሰኞ ታኅሳስ 6 ቀን 2013 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ ‹‹ሕዝባችንን ለበርካታ አሥርት ዓመታት በጠላትነት ፈርጆ ዘርፈ ብዙርዓታዊና መዋቅራዊ ግፍ ሲፈጽምበትና ሲያስፈጽምበት የቆየውን የትሕነግ አገዛዝ፣ ከኢትዮጵያ ለማስወገድ እልህ አስጨራሽ ትግል አድርጓል፡፡ ትሕነግ በአገር መከላከያ ሠራዊት ላይ ክህደትና አረመኔያዊ ግፍ በመፈጸም፣ አገሪቱን ለመበታተን ያደረገውን ሙከራ ለማክሸፍ ሕዝባችን ከፍተኛ ትግል አድርጓል፤›› ያለው አብን፣ ‹‹ይሁን እንጂ የሕዝባችንን ቅን ልቦናና ታጋሽነት፣ እንዲሁም የከፈለውን መስዋዕትነት ዋጋ የሚያሳጡና ከኢትዮጵያውያን ወገኖቹ ጋር በነፃነት፣ በእኩልነትና በፍትሕ የሚኖርባትን አገር ለመገንባት ያነገበውን ተስፋ ለማምከን እኩያን በጥምረት የተቀናጀ ጥቃት ከፍተውበታል፤›› ሲል አስታውቋል፡፡

አዋሽ ባንክ የጨረታ ማስታወቂያ

በአሁኑ ወቅት መንግሥት በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል ሕግና ሥርዓትን ለማስከበር የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለማደናቀፍና ሕወሓትን ከሞት መንጋጋ ፈልቅቆ ለማውጣት፣ ይህ ካልተሳካም የአፍራሽነትና የጥላቻ አጀንዳውን ለማስቀጠል፣ በቅንጅት የተሠለፉ ኃይሎች ቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልልን የሰብዓዊ ቀውስ ማዕከል እንዳደረጉት አብን በመግለጫው አስረድቷል፡፡ ‹‹በዚህ ጥቃት እየተሳተፉ ያሉ ፅንፈኛ የጥላቻ ኃይሎች በመካከላቸው መሠረታዊ የሆኑ የግብ ልዩነቶች ቢኖሯቸውም፣ በአማራና በአገው ሕዝባችን ላይ ያነገቡት የጥላቻና የጥፋት ፖለቲካ በጋራ እንዳሠለፋቸው ይታወቃል፡›› ሲልም አክሏል፡፡

በአማራና በአገው ሕዝብ ላይ እየተፈጸመ ያለው የዘር ማጥፋትና የዘር ማፅዳት ወንጀል መነሻ ምክንያቶችን መገንዘብ እንደሚያስፈልግ የገለጸው አብን፣ ስድስት ነጥቦችን ዘረዝሯል፡፡

እነሱም፣ ‹‹አንደኛ ትሕነግ በሕዝባችን ላይ በቀጥታ እንዲሁም በትርክት፣ በፖሊሲ፣ በመዋቅር፣ በሎጂስቲክስና በገንዘብ ዕገዛ እያደረገ ሲያስፈጽም መቆየቱ፣ ሁለተኛ መነሻው ፅንፈኞች በሕዝባችን ላይ ያላቸው ጥላቻ ሲሆን በዋናነት ሕዝቡን ማኅበራዊ ዕረፍት ለመንሳት የታለመ መሆኑን፣ ሦስተኛ ትሕነግ በጥላቻ፣ በአግላይነትና በአምባገነንነት የማዕከላዊ መንግሥት ሥልጣን መቆጣጠሩን ተከትሎ ወልቃይት፣ ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያን በኃይል ወደ ትግራይ በማካለል፣ ሌሎች የአማራ አካባቢዎችን ደግሞ በሕገወጥና በማናለብኝነት ወደ ተለያዩ ክልሎች እንዳካተታቸው ይታወቃል፡፡ በእነዚህ አካባቢዎች ውስጥ የሚኖረው ሕዝባችንም በሁሉም ዘርፎች የሚገለጹ ሰብዓዊ መብቶቹን ተገፎ፣ በተለይም አጠቃላይ ህልውናው አደጋ ላይ ወድቆ መቆየቱን፣ በመተከል የሚኖረው የአማራና የአገው ሕዝብ ወደ ነባር አማራዊ አስተዳደር ለመካለል ሕጋዊ የይገባኛል ጥያቄ አቅርቦ እንደሚገኝና ይኼን የመብት ጥያቄ ለማዳፈን ሰፊና የተቀናጀ ሴራ እየተተገበረ ነው፤›› በማለት በመግለጫው ገልጿል፡፡

‹‹አራተኛ እስካሁን በሕዝባችን ላይ በርካታ ተደራራቢ የዘር ማጥፋትና የዘር ማፅዳት ወንጀሎች የተፈጸሙ ሲሆን፣ ለመከላከልም ይሁን ጥፋተኞችን ተጠያቂ ለማድረግ የሚያስችል አገራዊና መንግሥታዊ ትጋት አለመኖሩ፣ አምስተኛ ዝቅተኛ የሆነውን ሕግ የማስከበርና ዜጎችን ከጥቃት የመከላከል መንግሥታዊ ግዴታን ካለመወጣት ባለፈ፣ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ በየእርከኑ የኃላፊነት ቦታዎችን የያዙ አመራሮችና ባለሥልጣናት ጥቃት ለሚሰነዝሩ ፅንፈኛ ኃይሎች ከለላ በመስጠትና በቀጥታ በመሳተፍ ጭምር ከፍተኛ የአፍራሽነት ድርሻ እንዳለቸው፣ ስድስተኛ ዛሬም የአማራ ሕዝብ ከሌሎች ወንድም ሕዝቦች ጋር በመሆን የአገሩን ሰላምና አንድነት ለማስጠበቅ መስዋዕትነት ከፍሎ ያገኘውን ድል ለመንጠቅ፣ አመድ አፋሽ ለማድረግና ሕዝባችንን በጠላትነት ፈርጆ ለመቀጠል የሚፈልጉ ኃይሎች፣ ከሚከተሉት የሕዝብአገት ፖለቲካ (Hostage Politics) ያልታቀቡ መሆኑን መረዳት ይገባል፤›› ሲል አብን አትቷል፡፡

የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል መስተዳድር የሰላምና ደኅንነት ተቋም ወደ ዘር ማጥፋት እርከን ተሸጋግሮ የቀጠለውን ሰፊ ጥቃት ለመከላከል የአቅም እጥረት ብቻ ሳይሆን ፍላጎትም እንደሌለው ፍንትው ብሎ የተገለጠ እውነታ መሆኑን የገለጸው አብን፣ የፌዴራል መንግሥትና የአማራ ክልላዊ መንግሥት በጋራ ሕዝቡን ለመከላከል የሚያስችል አስቸኳይ አቋም እንዲወስዱ ጥሪ አስተላልፏል፡፡

በመንግሥት በኩል የሕዝብን ሰላምና ደኅንነት ለማስከበር ቁርጠኝነት እስካለ ድረስ የአማራ ሕዝብ  ከጎኑ እንደሚቆም ያስታወቀው አብን፣ ‹‹ይህ ካልሆነ ግን ሕዝባችን ራሱን የመከላከል ተፈጥሯዊ መብቱን በመጠቀም ህልውናውን ለመታደግ፣ የጥፋት ኃይሎችን ለመመከት፣ ብሎም ለሕግ ለማቅረብ በፅኑ እንደሚታገል እናሳውቃለን፤›› ብሏል፡፡

በአማራ ማንነት ላይ ያነጣጠረን ጥቃት ለመከላከልና በዘላቂነት ለመቀልበስ መላው የአማራ ሕዝብ፣ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትና ሁሉም የአማራ የፖለቲካ ድርጅቶች የማያወላዳ የጋራ አቋም መውሰድና ተፈጻሚነት ያለው የፖለቲካና የደኅንነት እንቅስቃሴ በአስቸኳይ ሊያደርጉ ይገባል ሲልም አሳስቧል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ መተከል ዞን ቡለንና ድባጤ ወረዳዎች ውስጥ በነዋሪዎች ላይ በተደጋጋሚ ጥቃት ተሰንዝሮ በርካቶች መገደላቸውና መፈናቀላቸው ይታወሳል፡፡ በወረዳዎቹ ውስጥ ሰሞኑን በነዋሪዎች ላይ ግድያ መፈጸሙ ከአካባቢዎቹ የሚወጡ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ በአካባቢዎቹ ጥቃት የሚፈጽሙት የፀጥታ ኃይሎችን የደንብ ልብስ የለበሱ መሆኑም እየተነገረ ነው፡፡

በዞኑ የተሰማራው ኮማንድ ፖስት እሑድ ዕለት ኃላፊነታቸውን አልተወጡም በተባሉ 66 ያህል አመራሮችና የፖሊስ አባላት ላይ ዕርምጃ መወሰዱን፣ 50 ያህል ጥቃት ፈጻሚዎች መማረካቸውንና 43 ደግሞ እጅ መስጠታቸውን አስታውቋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

አወዛጋቢው የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ጉዳይ

በኢትዮጵያ የሕገ መንግሥት ማሻሻል ጉዳይ ከፍተኛ የፖለቲካ ውዝግብ የሚቀሰቀስበት...

 መፍትሔ  ያላዘለው  የጎዳና  መደብሮችን  ማፍረስ

በአበበ ፍቅር ያለፉት ስድስት ዓመታት በርካቶች በግጭቶችና በመፈናቀሎች በከፍተኛ ሁኔታ...

የተናደው ከቀደምቱ አንዱ የነበረው የአዲስ አበባ ታሪካዊ ሕንፃ

ዳግማዊ አፄ ምኒልክ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መገባደጃ መናገሻ ከተማቸውን...

የአከርካሪ አጥንት ሕክምናን ከፍ ያደረገው ‘ካይሮፕራክቲክ’

በአፍሪካ ከጀርባ ሕመም ጋር በተያያዘ በርካታ ሰዎች ለከፍተኛ የአካል...