የኢትዮጵያን ድንበር በመሻገር የእርሻ መሬቶችን የወረሩና አንለቅም ያሉ የሱዳን ወታደሮችን የገፉ የውጭ ኃይሎች እንዳሉ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዲና ሙፍቲ (አምባሳደር) ማክሰኞ ታኅሳስ 20 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንዳስታወቁት፣ ምንም እንኳን በሱዳን ውስጥ ያሉ የፖለቲካ ልሂቃንና ወታደራዊ አመራሮች ፍላጎት ያለ ቢሆንም፣ የኢትዮጵያንም ሆነ የቀጣናውን መረጋጋት የማይፈልጉ የውጭ ኃይሎች አሉ፡፡
እነዚህ ኃይሎች ከቀጣናው ትርምስ መጠቀም ፍላጎት እንዳላቸው፣ አትዮጵያ በዙሪያዋ ካሉ ጎረቤት አገሮች ጋር ብትናቆር እንጠቀማለን ብለው እንደሚያስቡና ለዚህም እንደሚሠሩ ያስታወቁት ዲና (አምባሳደር)፣ አሁን በሚታየው የሱዳንና የኢትዮጵያ ድንበር ግጭት ላይም በእጅ አዙር ተሳትፎ እያደረጉ ናቸው ብለዋል፡፡
ቃል አቀባዩ በስም ያልጠቀሷቸውና ይታወቃሉ ያሏቸው የውጭ ኃይሎች ቀድሞ ከነበሩ ቅኝ ገዥዎች ጋር በማበር፣ ሱዳንን የገዙና አሁንም ሕዝቡን እንደ ሕዝብ የማያዩ ናቸው ሲሉ ገልጸዋቸው፡፡ አሁንም ድረስ የሱዳንን ሰፊ መሬት ይዘው ያሉና ሕዝቡን እንደ ሰው የማይቆጥሩ ናቸው ብለዋቸዋል፡፡
የውጭ ኃይሎቹ በቁማርተኛነት የሚታወቁ ስለሆኑ እነዚህን የማጋለጥ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል በማለት፣ የሱዳን ሕዝብ እንዲያውቀው እንደሚደረግ አስረድተዋል፡፡ ‹‹ለእነሱ እጅ አንሰጥም፤›› ብለዋል፡፡ ሆኖም የእነዚህ ኃይሎች መጠቀሚያ የሆኑ አካላት በሱዳን መኖራቸውን አውስተዋል፡፡
የሁለቱ አገሮች ወዳጅነት ጠንካራ መሆኑን ያስታወሱት ዲና(አምባሳደር)፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የተመራ ልዑክ ወደ ሱዳን ካርቱም አቅንቶ ውይይት በማድረግ ሱዳን በቅርቡ ከአሸባሪ ደጋፊነት ዝርዝር በመሰረዟ ደስታውን ገልጿል ብለዋል፡፡ የሱዳን ሕዝብና መንግሥት በትግራይ ክልል በነበረው የሕግ ማስከበር ዘመቻ ለተሰደዱ ኢትዮጵያውያን ያደረጉትን ድጋፍ ልዑኩ በማድነቅ፣ በሁለቱ አገሮች ድንበር አካባቢ ያለው ድንበር የሚካለልበትን መንገድ ተወያይቷል ሲሉም አክለዋል፡፡
በሁለቱ ሕዝቦች መካከል ያለው ጠንካራ ግንኙነት በቀላሉ የሚፈርስ እንዳልሆነ በማስታወቅ፣ የድንበር ማካለሉ ሥራ ላለፉት 100 ዓመታት በተለያዩ ምክንያቶች ዕልባት ሳይሰጠው በመቅረቱ አሁን የተፈጠረው ችግር መከሰቱን አስገንዝዋል፡፡ የድንበር አካባቢ ችግር ተፈትቶ ወደ ቀድሞ ሁኔታ በቅርቡ እንደሚመለስም ተስፋቸውን ገልጸዋል፡፡
ይሁንና ይኼ ማለት የኢትዮጵያ ድንበርና ሉዓላዊነት ሲደፈር አርፎ መመልከት ማለት እንዳልሆነ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በዲፕሎማሲ ዘርፍ ያለውን ሥራ ሲያከናውን ከዱላው ይልቅ ካሮቱን ነው የሚጠቀመው ብለው፣ ‹‹ባለዱላውም ዱላውን የጣለ አይመስለኝም?›› ሲሉም አውስተዋል፡፡ ስለዚህም ኢትዮጵያ በሯን ከፍታ ቁጭ ያለች አይደለችም ብለዋል፡፡