ሁሉም በየፊናቸው ቁጭ ብለው ውዝግብ ውስጥ ገብተዋል፡፡ አንዳንዶቹ የያዙትን ሲጋራ ሲቀባበሉ ሌላዎቹ ደግሞ ከአፋቸው የማይለየውን ማስቲሽ ወደ አፍንጫቸው በመማግ ራሳቸውን ጥለዋል፡፡ የሚጠቀሟቸው አደንዛዥ ዕፆች የዕለት ከዕለት ተግባራቸው በመሆኑ የፊታቸውን ገጽታ ቀይሮታል፡፡ ከዛም አልፎ በጤናቸው ላይ ትልቁን ችግር ፈጥሯል፡፡ የሚጠቀሙት ዕፅ ከሱስ ባለፈ ራባቸውን የሚያስታግሱበት ነው፡፡
ከእርሱ መካከል ታዳጊው ሙሳ ራመቶ በጎዳና ላይ መኖር ከጀመረ ሦስት ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ በሻሸመኔ ከሚኖሩት ቤተሰቦቹ ጋር በመጋጨቱ ምክንያት ወደ ጎዳና ሕይወቱ የገባው፡፡ በአሁኑ ወቅትም ከጓደኞቹ ጋር በመሆን በቦሌ አካባቢ በተለያዩ ቦታዎች ላይ በመዘዋወር የሚተኛበትን ሥፍራ እያመቻቸ ኑሮውን እየገፋ ነው፡፡ የሚጠቀሙት አደንዛዥ ዕፆች ራሳቸውን ከረሃብና ከተለያዩ ነገሮች የሚከላከልላቸው መሆኑን የሚናገረው ሙሳ፣ የዕለት ጉርሳቸውንም ለማግኘት አላፊ አግዳሚ የሚሄዱ ሰዎችን ገንዘብ በመለመንና ከተለያዩ ሆቴል ቤቶች ትርፍራፊ በመቀበል እንደሚመገቡ አስረድቷል፡፡ አብዛኛውን ጓደኞቹም በእሱ ዕድሜ ክልል ላይ የሚገኙ በመሆናቸው በመተሳሰብ ያገኙትን ነገር እኩል ተካፍለው በመጠቀም የጎዳናት ኑሯቸውን እየገፉ ነው፡፡ በክረምቱ የሚያድሩበት ቦታ ለዝናብ ተጋላጭ በመሆኑና የሚረባ ልብስ እንኳን ስለማያገኙ በሚጠቀሙት ሱስ አማካይነት ራሳቸውን ከብርድ እንደሚከላከሉ ገልጿል፡፡ ‹‹ከዚህ በፊት ቤተሰብ ላይ እያለሁ የተመቻቸ ኑሮ ነበረኝ፡፡ አሁን ላይ ግን የጎዳና ሕይወትም ከመጠን በላይ አንገሽግሾናል፤›› ሲልም ምሬቱን ይገልጻል፡፡ ያለበትን ሱስ ሙሉ በሙሉ በመተው ወደ ቤተሰቦቹ ተመልሶና ከእናትና አባቱ ጋር መኖርና እነሱንም መርዳት እንደሚፈልግም ሳይናገር አላለፈም፡፡
ሌላኛው የጎዳና አዳሪ ታዳጊው አቢቾ ሶኮራ በዚህ ሕይወት ውስጥ መኖር ከጀመረ ሦስት ወራትን አስቆጥሯል፡፡ በሻሸመኔ አካባቢ በተከሰተው ግጭት ምክንያት የጎዳና ሕይወትን መቀላቀሉን የሚናገረው አቢቾ ከቤተሰቦቹ ጋር በነበረበት ጊዜ ትምህርቱንም በአግባቡ ይከታተል እንደነበር አስታውሷል፡፡
በአሁኑ ወቅት ሻሸመኔ ከነበሩ ጓደኞቹ ጋር አብሯቸው የሚኖረው አቢቾ ለጎዳና ሕይወት አዲስ በመሆኑ ምክንያት በጣም እንደ ከበደውና ከዚህ ቀደም የማይጠቀማቸው ሱሳ ሱሶች እየተጠቀመ በመሆኑ በሕይወቱ ላይ ትልቅ ሳንካ እንደፈጠረበት ተናግሯል፡፡
ጓደኞቹም የሚጠቀሟቸው አደንዛዥ ዕፆች ከዚህ በፊት ዓይቷቸው እንደማያውቅ ከነሱ ጋር በመሆን የጀመረውን ሱስ ገፍቶ ከቀጠለበት አሳሳቢ ነገር ውስጥ እንደሚገባ ይናገራል፡፡ በተለይም ሌሊት ሌሊት ላይ ብርዱ በጣም ከባድ በመሆኑ ምክንያት አደንዛዥ ዕፆችን እንደሚጠቀሙ ገልጾ፣ ከዚህ በኋላም የተሻለ ሕይወት ለመኖርም ከዚህ ሱስ መላቀቅ አለብኝ ይላል፡፡ ለዚህም ድጋፍ ይሻል፡፡
‹‹አንዳንዴም የሚላስና የሚቀመስ ነገር ስናጣ በሱስ አማካይነት ራባችንን እናስታግሳለን፤›› የሚለው አቢቾ ይህንን የጎዳና ሕይወት ትቶ ወደ ቤተሰቦቹ መመለስና ያቋረጠውን ትምህርት መጀመር የሁልጊዜ ምኞቱ መሆኑን ከመግለጽ አልተቆጠበም፡፡
በአሁኑ ወቅትም በተለያዩ ችግሮች ምክንያት የጎዳና ተዳዳሪዎች ቁጥር እየተንሰራፋ በመምጣቱ ምክንያት በፒያሳ፣ በቦሌ፣ በቦሌ ሚካኤል፣ በስታዲየም፣ በመገናኛ፣ በሳሪስና በካዛንችስ አካባቢዎች ላይ ኑሯቸውን አድርገው ይታያል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ የማኅበራዊ ደኅንነት ልማት ማስፋፊያ ዳይሬክተር ወ/ሮ አበበች ጥላሁን ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከተለያዩ ቦታዎች ላይ እየፈለሱ የመጡ የጎዳና ተዳዳሪዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ ትልቅ ችግር እንደፈጠረባቸው አስረድተዋል፡፡
የጎዳና ተዳዳሪዎችን ቁጥር ለመቀነስ በ2013 ዓ.ም. አምስት ወራት ውስጥ በአንደኛው ዙር በመስቀልና በኢሬቻ በዓላት አጋጣሚ በአሥሩም ክፍለ ከተሞች ከጎዳና የተነሱት 3,506 ሲሆኑ፣ በሁለተኛው ዙር ደግሞ ከሁሉም ክፍለ ከተሞች 4,780 በአጠቃላይ 8,286 የጎዳና ተዳዳሪዎች ተነስተዋል፡፡ ከነዚህ መካከል ከቤተሰብ የተቀላቀሉ፣ የሥነ ልቦና ክህሎት ሥልጠና አጠናቀው የሙያ ክህሎት ሥልጠና የጀመሩ የጎዳና ተዳዳሪዎች እንደሚገኙበት ወ/ሮ አዳነች ገልጸዋል፡፡
በ2012 ዓ.ም. ላይ ባገለገሉ የከተማ አውቶቡሶች ላይ ጥቃቅንና አነስተኛ ንግድ ላይ ተደራጅተው ወደ ሥራ የተሰማሩ እንዳሉና በአሁኑ ወቅትም ይህንን ታሳቢ በማድረግ የተለያዩ ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑንም አክለዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮም የሥራ ትስስሮችን በመፍጠር ወደ ሥራ እንዲገቡ የተደረገላቸው በርካታ የጎዳና ተዳዳሪዎች እንዳሉ አስታውሰዋል፡፡
የጎዳና ተዳዳሪዎች ወደ ማቆያ ማዕከል የሚገቡት በራሳቸው ፈቃድ ሲሆን፣ ቁጥራቸው ያነሰው በርካቶች ፈቃደኛ ባለመሆናቸው መሆኑን ወ/ሮ አበበች ሳይጠቅሱ አላለፉም፡፡ ሆኖም እነሱን የማንሳት ሒደትን ቀጣይነት ባለው መልኩ የሚሠራ ይሆናል ብለዋል፡፡
ዓምና ለ200 የጎዳና ተዳዳሪዎች ከኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ ካምፓኒ፣ አዲስ ብድር ቁጠባና ኤሊኤንሲ ጋር በመተባበር የተለያዩ የሙያ ሥልጠናዎችን መሰጠቱንና ሃያ ማኅበሮች መቋቋማቸውን ይታወሳል፡፡ 35 የሚሆኑ በግል ተደራጅተው ከወጣቶች ተዘዋዋሪ ፈንድ ተጠቃሚ በመሆን ሥራ በመጀመር ከማኅበረሰቡ ጋር ሲቀላቀሉ 40 ዎቹ ደግሞ በመንገድ ትራንስፖርትና በአዋሽ ወይን ጠጅ ድርጅት የሥራ ዕድል በማግኘታቸው ራሳቸውን እንዲችሉ ተደርጓል፡፡
የጎዳና ተዳዳሪዎች ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ ፍሰቱ እየጨመረ በመምጣቱ መንግሥት ግንባታዎችን በማስገንባት ተደራሽ ሥራዎችን እየሠራ ቢገኝም ሕፃናት፣ ሴቶችና ሌሎች የማኅበረሰብ ክፍሎችን ከጎዳና ሕይወት ማንሳት ለመንግሥት ብቻ እንደማይተው የሚጠቁሙ አሉ፡፡