ከዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት በኢትዮጵያ የቆላ ዝንብን ለመካላከል እንዲያግዙ ወደ አገር የገቡ ሁለት ሰው አልባ አውሮፕላኖች፣ በአገር ውስጥ መመርያ ባለመኖሩ ምክንያት በሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ተይዘው ያለ ሥራ ለሦስት ዓመታት መቆማቸው ተነገረ።
የኢትዮጵያ የቆላ ዝንብና የገንዲ በሽታ መቆጣጠሪያ ተቋም፣ የቆላ ዝንብን በእጅጉ ለመካለከል ያግዘኛል ያላቸውንና ከተቋሙ የተሰጡትን ሰው አልባ አውሮፕላኖች፣ እንዴት ማንቀሳቀስ እንደሚቻል የሚፈቅድ መመርያ ይውጣ በማለት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ጠይቋል።
የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ዳኛቸው በየነ (ዶ/ር) ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ችግሩን ለመፍታት ያልተሞከረ ጥረት እንደሌለና በግብርና ሚኒስቴር በኩልም ጥረት ቢደረግም፣ በሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን በኩል ከደኅንነት ጋር በተገናኘ ለዓመታት የተያዙትን አውሮፕላኖች ወደ ሥራ ማስገባት አልተቻለም።
የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት በአፍሪካ በቆላ ዝንብ ከተወረሩ አገሮች ኢትዮጵያን እንደ ማዕከል ቆጥሮ በመጀመርያ የሰጠ ቢሆንም፣ አውሮፕላኖቹን ወደ ሥራ ማስገባት ባለመቻሉ የፓርላማውን ዕገዛ እንደሚሹ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
‹‹የአርብቶ አደሮችን የቁም እንስሳት በከፍተኛ ሁኔታ እየጎዳ የሚገኘውን የቆላ ዝንብ ለማስወገድ፣ የሚያግዙት አውሮፕላኖች ተንቀሳቅሰው እንዲሠሩ የሚፈቅድ ሕግ እንዲዘጋጅልን እንጠይቃለን፤›› ሲሉ ዋና ዳይሬክተሩ ጠይቀዋል።
የገንዲ በሽታ አብዛኞቹን የቁም እንስሳትን የሚያጠቃ ሲሆን፣ በሽታውን የሚያስተላልፈው የቆላ ዝንብ በተለይም በምዕራብ ኢትዮጵያ በእንስሳት ላይ ቀላል የማይባል ችግር እየፈጠረ ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፣ በበሽታው የተጠቁ እንስሳት ምንም ዓይነት ጥቅም አይሰጡም ሲሉ አስረድተዋል።
እንደ ዳኛቸው (ዶ/ር) ወደ አገር ቤት የገቡት ሰው አልባ አውሮፕላኖች የሴትና የወንድ የቆላ ዝንቦች በቤተ ሙከራ በማራባትና ወንዶችን በመለየት በጨረራ አማካይነት በማምከን፣ የመከነውን ዝርያ ወደ ጫካ ወስዶ በመልቀቅ እንዳይራቡ ለማድረግ ጥቅም ይሰጣሉ።