በመስቀል አደባባይ ፕሮጀክት ግንባታ ምክንያት 700 ሚሊ ሜትር ስፋት ባለው የውኃ መስመር ላይ ሰኞ ጥር 3 ቀን 2013 ዓ.ም. ማለዳ አካባቢ ጉዳት መድረሱን የአዲስ አበባ ከተማ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን አስታወቀ፡፡
ሲሲሲሲ የተባለ የቻይና ሥራ ተቋራጭ ለውኃ መስመሩ ጥንቃቄ ሳያደርግ የግንባታ ሥራ ሲያከናውን በነበረበት ወቅት በደረሰ የውኃ መስመር ፍንዳታ ምክንያት ችግሩ ማጋጠሙን ተገልጿል፡፡
በደረሰው ጉዳት ምክንያት ጋንዲ ሆስፒታል፣ ቤተዛታ ሆስፒታል፣ ኢትዮጵያ ሆቴል፣ አምባሳደር አካባቢ፣ ቦሌ መንገድ እስከ ደንበልና በአጠቃላይ ስታዲየም ዙሪያ ያሉ አካባቢዎች የውኃ አገልግሎት እንደተቋረጠባቸውም ታውቋል፡፡
የባለሥልጣኑ የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊ ወ/ሮ ሰርካም ጌታቸው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ መስመሩን በሁለት ቀናት ውስጥ ጠግኖ ወደ መደበኛ ሥርጭት ለማስገባት ርብርብ እየተደረገ ነው፡፡
በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች ችግሩ በተደጋጋሚ እየገጠማቸው እንደሆነ የገለጹት ኃላፊዋ፣ በዋነኝነት ብዙዎቹ ግንባታ የሚያከናወኑ አካላት ያለ ምንም ቅደመ ጥንቃቄ ሲቆፍሩ እንደሚታዩና አንዳንዶቹም መስመሮቹ ላይ ጉዳት ካደረሱ በኋላ ከሥፍራው እንደሚጠፉ አስረድተዋል፡፡
‹‹ደጋግመው እየሰበሩ የሚያስቸግሩን ድርጅቶች አሉ፤›› ያሉት ኃላፊዋ፣ ቁፋሮ የሚያካሂዱ አካላት፣ ውኃ መሬት ውስጥ ያለ ሀብት በመሆኑ በአገር ሀብት ላይ ጉዳት ከማድረስ በፊት ጥንቃቄ በተሞላበት ሁኔታ እንዲሠሩ አሳስበዋል፡፡
በመስቀል አደባባይ ያጋጠመው ከአቃቂ ከርሰ ምድርና ከለገዳዲ ግድብ የሚመጣው ውኃ የሚገናኝበት ሥፍራ እንደሆነ አክለውም ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የመስቀል አደባባይ ፕሮጀክት በውኃ ተጥለቅልቋል፡፡