የሱዳን መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናትና የጦር አዛዦች ወደ ካይሮ በመጓዝ በኢትዮጵያና በሱዳን አዋሳኝ ድንበር ከሰሞኑ ስለተከሰተው ወታደራዊ ውጥረት፣ ለግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ማስረዳታቸውን የአገሪቱ የመንግሥት የዜና ወኪል ገለጸ።
ወደ ካይሮ ካመራው የሱዳን ከፍተኛ ልዑክ ውስጥ ከተካተቱት ባለሥልጣናት መካከል የአገሪቱ የባህልና ማስታወቂያ ሚኒስትሩ ፈይሰል ሞሐመድ ሳላህ የሚገኙበት ሲሆን፣ የጦር ኃይሉን በመወከል ደግሞ ሌተና ጄኔራል ሻምስ አል ዲን ካባሺ መጓዛቸውን መረጃው ያመለክታል።
የልዑካን ቡድኑ ሐሙስ ታኅሳስ 6 ቀን 2013 ዓ.ም. በግብፅ ካይሮ መዲና ያደረገውን ቆይታ አጠናቆ ወደ ሱዳን መመለሱን የሚገልጸው የዜና ወኪሉ ሱና፣ በቆይታቸውም ከፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ጋር ተገናኝተው በኢትዮጵያና በሱዳን አዋሳኝ ድንበር ላይ ስለተከሰተው ውጥረት ማብራሪያ ማቅረባቸውን ዘግቧል፡፡
ወደ ካይሮ ያመራው የሱዳን መንግሥት ከፍተኛ ልዑክ በኢትዮጵያና በሱዳን መካከል ያለው የድንበር ጉዳይ፣ ሁለቱ አገሮች እ.ኤ.አ. በ1902 እና በ1972 ባደረጉዋቸው ስምምነቶች፣ እንዲሁም እነዚህን ስምምነቶች መሠረት አድርገው በተካሄዱ የጋራ ውይይት ቃለ ጉባዔ ሰነዶች አማካይነት መፍትሔ እንደሚያገኙ ማስረዳቱን፣ የባህልና ማስታወቂያ ሚኒስትሩ መግለጻቸውን የዜና ወኪሉ ባወጣው ዘገባ አመላክቷል።
ሱዳን በስተምሥራቅ በኩል ከኢትዮጵያ በምትዋሰንበት አካባቢ የጦር ኃይሏን ያሰማራችው ድንበሯን ለመጠበቅና የዜጎቿን ደኅንነት ለማረጋገጥ ብቻ መሆኑን ሚኒስትሩ መናገራቸውን፣ ሱዳን ከኢትዮጵያም ሆነ ከሌላ አካል ጋር ወደ ጦርነት መግባት እንደማትፈልግ መግለጻቸው ተጠቁሟል።
በኢትዮጵያና በሱዳን መካከል ያለው የድንበር ጉዳይ በሰላማዊ መንገድ በውይይት እንደሚፈታ እምነታቸውን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ‹‹ሱዳን ተገዳ ካልሆነ በስተቀር ምንም ዓይነት ወታደራዊ ዕርምጃ የመወሰድ ፍላጎት የላትም፤›› ማለታቸው ተገልጿል፡፡
ወደ ካይሮ ያመራው ልዑክም የድንበር ጉዳዩን ለመፍታት በኢትዮጵያና በሱዳን የተቋቋመው የድንበር ኮሚሽን ሲያደርጋቸው ስለነበሩ ውይይቶች ለግብፅ ፕሬዚዳንት ማስረዳቱን፣ ይኼው ኮሚሽን በሚያደርጋቸው ቀጣይ ውይይቶች ችግሩ መፍትሔ ያገኛል የሚል እምነት በሱዳን በኩል ስለመኖሩ መግለጻቸውንም መረጃው አመልክቷል።
የድንበር ውዝግቡ ከሚነሳባቸው አካባቢዎች አንዱ በሆነው አልፋጋሽ ድንበር በኢትዮጵያ በኩል ያለው እንቅስቃሴ እንደሚባለው የአርሶ አደሮች ወይም የሚሊሻዎች እንዳልሆነ የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ የሱዳን መንግሥት ከኢትዮጵያ በኩል የሚቃጣ ጥቃትን ለመመከት ዝግጁ መሆኑን አስታውቀዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የሱዳን ሲቪል አቪዬሽን አልፋጋሽ በሚባለው የኢትዮጵያ ድንበር አካባቢ የሚገኘውን የአየር ክልል ለአየር በረራ ዝግ ማድረጉን አስታውቋል።
የሱዳን ሲቪል አቪዬሽን መሥሪያ ቤት የተገለጸውን የአየር ክልል ለመዝጋት ምክንያት የሆነው፣ የኢትዮጵያ መንግሥት አየር ክልሉን ጥሶ በረራ አድርጓል በሚል ነው።
የአየር ክልሉ መዘጋቱ ከመገለጹ አንድ ቀን ቀደም ብሎ በአካባቢው በረራ ሲያደርግ የነበረ የሱዳን ሔሊኮፕተር መከስከሱን መረጃዎች አመልክተዋል።
በሌላ በኩል የሱዳን ባለሥልጣናትና ምሁራን በኢትዮጵያና በሱዳን ድንበር በተመለከተ ሰሞኑን ባካሄዱት ምክክር፣ የሱዳን ታሪካዊ ወሰን የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ የሚገነባበትን የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል አካባቢ እንደሚያካትት አውስተዋል።
ይህም በርካታ ኢትዮጵያውያንን አስቆጥቷል። በተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሱሌማን ደደፎ የሱዳን ልሂቃን የህዳሴ ግድቡ የሚገነባበትን አካባቢ የሱዳን የግዛት አካል እንደሆነ መግለጻቸውን በመቃወም፣ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሠፈሩት መልዕክት፣ ‹‹… ይገባናል፡፡ እያሉ ያሉት በቀጥታ የህዳሴ ግድቡን ሲሆን፣ በዚህም አላዋቂነታቸው ከመጠን ያለፈ መሆኑን አስመስክረዋል። ይህም አገሬን ለሚለው ኢትዮጵያዊ ዜጋ ሁሉ በቂ መልዕክት የሚያስተላልፍ ይመስለኛል፤›› ብለዋል።
አክለውም፣ ‹‹የሱዳን መንግሥት ይገባኛል የሚለውን ድንበር በሰላማዊ መንገድ መጠየቅ ሲችል ለምን በኃይል ለመቆጣጠር እንደፈለገና ለምን ኢትዮጵያ ውስጣዊ ችግር ላይ ያለችበትን ወቅት ለምን እንደመረጠ ራሱን መጠየቅ አለበት፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡
‹‹ግብፅ ኢትዮጵያ በውስጥ ጉዳዮች ችግር ላይ መሆኗን በማየት፣ የህዳሴ ግድቡን አሁን ማስቆም ካልቻልኩ መቼውንም ማስቆም አልችልም በማለት፣ ሱዳንን በእኛ ላይ ማዝመቷ ሳያንስ፣ አሁን ጭራሽ መተማና የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል ይገባኛል ማለቷ አስቂኝ ነው፤› ሲሉም በሁለቱ አገሮች መካከል ያለውን ጥምረት ገልጸውታል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዲና ሙፍቲ (አምባሳደር) የተፈጠረውን ችግር በወይይት መፍታት የኢትዮጵያ አማራጭ እንደሆነ፣ ነገር ግን በሱዳን በኩል አሁንም በኃይል ድንበር የመቆጣጠርና የማጥቃት እንቅስቃሴ መኖሩን አመልክተው፣ ነገሩ ከልክ ካለፈ ኢትዮጵያ ዕርምጃ ልትወስድ እንደምትችል መግለጻቸው አይዘነጋም።