የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከመጪው ምርጫ በፊት የመንግሥት ተቋማትን የሚያቋቁሙና የኃላፊነት ሽግሽግ ሊያደርጉ የሚችሉ አዋጆችም ሆኑ ደንቦች፣ ለፓርላማ ተመርተው እንዳይፀድቁ መመርያ መተላለፉ ተሰማ።
በ1997 ዓ.ም. ምርጫ ወቅት በተለይ ገዥው ፓርቲ (ኢሕአዴግ) በአዲስ አበባ ከተማ መሸነፉን ሲሰማ በአስተዳደሩ ሥር የነበሩ ሥልጣንና ኃላፊነቶችን ሰብስቦ ወደ ፌዴራል መንግሥት የወሰደበት ዓይነት አሠራር አንዳይፈጠር በሚል ሥጋት፣ የቀረቡ አዋጆችና ደንቦች ከምርጫ በኋላ ይደረጉ የሚል አቋም መያዙን፣ ምክትል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አቶ ተስፋዬ ዳባ ለሪፖርተር አስረድተዋል።
በመሆኑም ተመሳሳይ ዓይነት ስህተትና ችግር እንዳይፈጠር ተብሎ፣ ለጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ለአስተያየት የሚመጡ የማቋቋሚያ አዋጆችና ደንቦች ባሉበት እንዲቆዩና ለፓርላማ እንዳይተላለፉ እየተደረገ ነው ብለዋል።
እንደ ምክትል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ ገለጻ፣ በአሁኑ ጊዜ በጣም አስፈላጊና በልዩ ሁኔታ መታየት ካለባቸው እንደ የኢትዮ ቴሌኮም ማቋቋሚያ አዋጅ ዓይነት ካልሆኑ በስተቀር፣ ሌሎች አዋጆችና ደንቦችን የማየት ዕደሉ ጠባብ ነው፡፡
ይህም ሊሆን የቻለው ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሊተላለፉ የነበሩ በርከት ያሉ አዋጆች፣ ከምርጫ በኋላ የሚቋቋመው አዲሱ መንግሥት ይያቸው በሚል አቋም እንደሆነ አቶ ተስፋዬ ገልጸዋል።
በመሆኑም ማንኛውም ዓይነት ተቋም ባለው ቁመና ሥራውን እያከናወነ እንዲቆይ ተደርጎ፣ የምርጫ ሥራ ላይ ብቻ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባ ስምምነት ላይ ተደርሷል ብለዋል።
መሥሪያ ቤቶችን ማሻሻል፣ ሥልጣንን የማስፋት ወይም የማጥበብ፣ ስም የመቀየር፣ እንዲሁም ተጠሪነትን የመቀየር ዓይነት አዋጆች ከምርጫ በኋላ የሚቋቋመውና አዲሱ መንግሥት ያስፈጽማቸው ተብለው በይደር መቀመጣቸውን አክለው ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ስድስተኛው ጠቅላላ ምርጫ ግንቦት 28 ቀን 2013 ዓ.ም.፣ የድምፅ መስጫ ቀን እንዲሆን የምርጫ ሰሌዳውን ማፅደቁ የሚታወስ ነው።