ቁጥራቸው 25 የሚደርሱ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች፣ መንግሥት ግጭት በተከሰተባቸው አካባቢዎች በሴቶችና ሕፃናት ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት እንዲያስቆም ጥሪ አቀረቡ፡፡
የሰላም ዕጦት በተከሰተባቸው አካባቢዎችና የአስቸኳይ ጊዜ ድጋፍ በሚሹ ቦታዎች ዓለም አቀፋዊ መርሆዎች ሳይሸራረፉ መተግበርና ተፈጻሚነታቸውን መከታተል ፈታኝ በመሆኑ፣ ከመኖሪያቸው የተፈናቀሉ ሰዎች በተለይም ሴቶችና ሕፃናት ለተለያዩ ጉዳቶች ተጋላጭነታቸው ከፍ ብሏል ብለዋል፡፡
በመሆኑም መንግሥት ከትግራይ ክልልም ሆነ ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ተፈናቅለው በስደተኛ ጣቢያ የሚኖሩ ዜጎች የሚደርስባቸውን ጥቃት በማስቆም፣ ሕግ የማስከበር ኃላፊነቱን ይወጣ ሲሉ ድርጅቶቹ በመግለጫቸው ጠይቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሴቶች ማኅበራት ንቅናቄ ዳይሬክተር ወ/ሮ ሳባ ገብረ መድኅን እንዳሉት፣ በትግራይ ክልል የሕግ ማስከበሩ ሒደት ከመደረጉ በፊት ነገሮች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ጥሪ አቅርበው ነበር፡፡ ‹‹ነገር ግን ይህ ሳይሆን ቀርቶ ከፍተኛ የሆነ የዜጎች መፈናቀል ተከስቷል፡፡ እሱም በሒደት ላይ እያለ በቤንሻንጉል ጉምዝ ሌላ ችግር በመከሰቱ እንደ ሲቪል ማኅብረሰብ ድርጅት ለችግሩ ዕርዳታና ድጋፍ ለማድረግ ተረባርበናል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹እኛ ሰላማዊ ዜጎችን የምንወክል ድርጅቶች ነን›› የሚሉት ወ/ሮ ሳባ፣ ‹‹ይኼን መግለጫ የምንሰጠው እንዲህ ብለው መግለጫ አወጡ ለማለት ሳይሆን፣ እያንዳንዱ የሚመለከተው አካል ግጭት በደረሰባቸው አካባቢዎች ተጠያቂነት እንዲሰፍን፣ መንግሥት ሕግ የማስከበርና የዜጎችን ሰላምና ደኅንነት የማስጠበቅ ኃላፊነቱን በአግባቡ እንዲወጣ ጥሪ ለማቅረብ ነው፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡
በትግራይ ክልል የሕግ ማስከበር ሥራ ከተከናወነ በኋላ በሴቶችና በሕፃናት ላይ የአስገድዶ መድፈር ጥቃት በሰፊው እየደረሰ መሆኑን፣ በአካባቢው ዝርፊያና ሌሎች ግጭቶችን ተገን በማድረግ የሚፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መኖራቸውን ለማወቅ ተችሏል ያለው ጥምረቱ ‹‹የኢትዮጵያ መንግሥት፣ ዓለም አቀፍና አገር በቀል ድጋፍ ሰጪዎች፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች፣ የግሉ ዘርፍ፣ የሚዲያ ተቋማትና ባለሙያዎች በሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ላይ ክትትል እንዲያደርጉና ለጉዳቱ አስፈላጊውን ትኩረት እንዲሰጡ እንጠይቃለን፤›› ብሏል፡፡