በአገሮችም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎና ብሎም የመምራት ዕድልና መብት እክሎች የበዙበት ነው፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሴቶችን ወደ ውሳኔ ሰጪነቱ ለማምጣት ትኩረት አግኝቶ እየተሠራ ቢሆንም፣ የሚፈለገውን ያህል ለውጥ ለማምጣት አልተቻለም፡፡ ዩኤን ውሜን ይፋ ያደረገው ዳሰሳ እንደሚያሳየውም፣ ሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ አሁን ባለበት አዝጋሚ ሒደት ከቀጠለ፣ በአገሮች ደረጃ ሴቶች በሕግ አውጪነት መሳተፍ ከ2063 በፊት አያሳይም፡፡ በሚኒስትርነት ዕርከን ከ2077 እንዲሁም በከፍተኛ የሥልጣን ዕርከን መያዝም ከ2150 በፊት እንደማይሆን ተንብየዋል፡፡
በተለያዩ ዘርፎች የተወሰኑ ለውጦች ቢታዩም ሴቶች አሁንም በመራጭነት፣ በመምራት፣ በውሳኔ ሰጭነት፣ በተመረጡበት ቢሮም ይሁን በሲቪል አገልግሎት፣ በግል እና በትምህርት ዘርፎች ያላቸው ውክልና አነስተኛ ነው፡፡
ይህ የሚሆነው ደግሞ ሴቶች የመምራት ለውጥ የማምጣት አቅም ስለሌላቸው አይደለም፡፡ በዴሞክራቲክ መንግሥት እኩል የመሳተፍ መብትም ቢኖራቸውም በሴቶች ላይ በሚፈጠሩ ጫናዎች ውክልናቸው አነስተኛ ነው፡፡
እንደ ዩኤን ውሜን ዳሰሳ፣ ሴቶች በፖለቲካ ለመሳተፍ በርካታ እክሎች ይገጥሟቸዋል፡፡ እክሎቹ በተቋማት በሚገኙ አግላይ ሕጎች የሴቶችን ተሳትፎ በሚገድቡ መሥፈርቶች ምክንያት የሚከሰቱ ናቸው፡፡ የሴቶች የመማር ዕድል በአካባቢያዊ ልማድ የተተበተበ በመሆኑ ከወንድ እኩል አለመማራቸው የችግሩ መሠረት ነው፡፡ ይህ ደግሞ በፖለቲካው ለመሳተፍ ወሳኝ የሆነውን ተግባቦት ለመፍጠርም ሆነ ገቢ ለማግኘት እንቅፋት ነው፡፡
ሴቶች በዓለም አቀፍ ደረጃ የፖለቲካ ተሳትፏቸውን ያቆረቆዘው የሚታዩበት መነጽር፣ ዝቅተኛ የትምህርት ደረጃና ለጤና ተደራሽ አለመሆን ነው ያለው ጥናቱ፣ በግለሰብ ደረጃ ሴቶች የተለያዩ ችግሮችን አልፈው ለመምራትና ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችሉ ደረጃዎች ላይ ቢደርሱም፣ አብዛኛው የዓለም ሴቶች ለዚህ አልበቁም፡፡ በመሆኑም የመወዳደሪያ ሜዳዎች ለሰዎች ሁሉ እኩል መሆን አለባቸው፣ ዕድሎችም ለሁሉም በእኩል ክፍት ሊሆኑ ይገባል ሲል አሥፍሯል፡፡
በመጋቢት ወር ለአሥር ቀናት ከሚካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት 65ኛ የሴቶች ሁኔታ ጉባዔ አስቀድሞ ዩኤን ውሜን ያደረገው ዳሰሳ፣ ሴቶች ከቀደሙት ጊዜያት በተሻለ በኑሮና በፖለቲካው የተሻለ ተሳትፎ ቢኖራቸውም፣ እኩልነት ወደኋላ መቅረቱን አመላክቷል፡፡
ዳሰሳው እንደሚያሳየው፣ ሴቶች የአገር መሪ የሆኑባቸው አገሮች 21 ናቸው፡፡ 119 አገሮች ደግሞ ሴት መሪ ኖሯቸው አያውቅም፡፡ 50 በመቶ የካቢኔ አባሎቻቸውን ሴት ያደረጉ አገሮችም 14 ብቻ ናቸው፡፡ የሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ በዚሁ ከቀጠለ ደግሞ ለቀጣይ 130 ዓመት ከሚፈለገው የፆታ እኩልነት መድረስ አይቻልም፡፡
ሆኖም የሴቶች በምርጫ መሳተፍና መመረጥ የሚወጡ ፖሊሲዎች የተመጣጠኑና የማኅበረሰቡን ፍላጎት ለመመለስ ያስችሉ ነበር፡፡ ያልተወከሉ ሴቶች ማለትም በገጠር የሚኖሩ፣ አካል ጉዳተኞችና የየአካባቢውን ነባር ነዋሪዎች ችግር ለመፍታትም ዓይነተኛ ሚና ይጫወቱ ነበር፡፡
ሴቶች ለማኅበረሰቡ ለውጥ የሚያመጡ ውሳኔዎችን ለማሳለፍ ቁልፍ ሚና ቢኖራቸውም፣ በሥራ ላይ ወይም ሕዝብ ፊት ለፊት ሲወጡ የሚደርስባቸው ጥቃት ሴቶች ወደ ሥልጣን እንዳይመጡ አድርጓል፡፡
በተለይ በበይነ መረብ በሴቶች ላይ የሚደርስ ጥቃት በመንግሥት የሥራ ኃላፊነት ላይ ያሉ ሴቶችን ዝም ለማስባል ጥቅም ላይ እየዋለ ነው፡፡ የሳይበር ጥቃት የሴት መብት ተሟጋቾችና የሴታዊነት ቡድኖችን ዝም ለማስባልም ጥቅም ላይ ውሏል፡፡
ዳሰሳ ከተደረገባቸው በፓርላማ የተወከሉ ሴቶች መካከል 80 በመቶ ያህሉም በሥራ ላይ እያሉ ሥነ ልቦናዊ ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል፡፡ ከሦስት አንዷ የኢኮኖሚ ከአራት አንዷ አካላዊ ጥቃትና ከአምስት አንዷ ፆታዊ ጥቃት አጋጥሟቸዋል፡፡ ከወንዶች ይልቅም ያልተገባ አቀባበልና ጥቃት ይገጥማቸዋል፡፡
በዓለም አሥር ሴት ርዕሰ ብሔሮች ሲኖሩ፣ 13 አገሮች ደግሞ በሴት ርዕሰ መንግሥት ይመራሉ፡፡ 21 በመቶ ሚኒስትሮችም አሉ፡፡ ዓመታዊ የሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ ዕድል ደግሞ 0.52 በመቶ ነው፡፡
በሴቶች ሚኒስትርነት የሚመሩት የተለመዱ አምስት ዘርፎችም፣ ይህ ሕፃናትን፣ ወጣቶችን፣ አዛውንቶችንና አካል ጉዳተኞን ያጠቃለለው ቤተሰብ፣ ማኅበራዊ ጉዳይ፣ የአካባቢ፣ ሥራ ቅጥርና የሴቶች ጉዳይ ናቸው፡፡
ዩኤን ውሜን ችግሩን ለመቅረፍ እየሠራ ሲሆን፣ አገሮችም ሴቶች ከከፍተኛ የሥልጣን እርከን እንዲደርሱና ውሳኔ መስጠት ላይ እንዲሳተፉና እንዲሠሩም ጥሪ አቅርቧል፡፡