የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በዕውን ወደ መሬት የሚያወርደው ከሆነ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ የዘመናት ጥያቄ መፍትሔ ሊሆን የሚችል ከ15 ዓመት በታች ፓይለት ፕሮጀክት ከሰሞኑ ይፋ አድርጓል፡፡ ጥር 28 ቀን 2013 ዓ.ም. ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በተደረገው ውይይት ላይ እንደተገለጸው፣ ፕሮጀክቱ በተመረጡ ቦታዎች ተግባራዊ ይደረጋል፡፡
ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ውጤታማነት በትልቁ እንደ ክፍተት ከሚታዩ ተግዳሮቶች አንዱ፣ ክለቦች የሚመሠረቱባቸው ዕሳቤዎችና ግባቸው ግልጽና የሚጣጣሙ አለመሆናቸው ነው፡፡ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑን ጨምሮ ቀደምት ክለቦች በዋናነት ግብ አድርገው ሲንቀሳቀሱ የሚታዩት ለጊዜያዊ ውጤት እንጂ፣ እንደ ሌሎች አገሮች ዘርፉን እንደ አንድ የልማት አማራጭ አድርገው በመመልከት ለተግባራዊነቱ መንቀሳቀስ አለመቻላቸው እንደሆነ ይወሳል፡፡
“ፕሪሚየር ሊግ” በሚል የተውሶ ስም ከሁለት አሠርታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረውን የሊግ አደረጃጀት ጨምሮ በኢትዮጵያ በየደረጃው የተዋቀሩ የእግር ኳስ ቡድኖች አሉ፡፡ ቡድኖቹ ከተመሠረቱበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን የያዟቸው ተጨዋቾች በሌሎች አገሮች እንደሚታየው በዕድገት ደረጃቸው ልክ ማግኘት የሚገባቸውን ከሥልጠና ጀምሮ እስከ አመጋገብ ተሟልቶላቸው ሳይሆን፣ አጋጣሚና ሁኔታዎች በፈቀዱላቸው ልጆች ጭምር መሆኑ በእያንዳንዱ ቡድን ውስጥ የሚገኙ ዕድሜ ጠገብ ተጨዋቾችን መመልከቱ ብቻ ሳይሆን፣ ውጤታቸው ጭምር በቂ ማሳያ ይሆናል፡፡
በመሆኑም ከዚህ በፊት ብሔራዊ ፌዴሬሽኑም ሆነ ሌሎች ይመለከተናል የሚሉ ባለድርሻ አካላት ተመሳሳይ ፓይለት ፕሮጀክቶች እንደሚከፈቱ በይፋ ከተነገሩ በኋላ፣ የፕሮጀክቶቹ ሰነዶች የመደርደሪያ ማድመቂያ ሆነው የቀሩበት ጊዜ ብዙ ከመሆኑ አንፃር፣ ይህ የዛሬው ፓይለት ፕሮጀክትም ተመሳሳይ ዕጣ ፈንታ እንዳይገጥመው የሚጠራጠሩ አልጠፉም፡፡
ባለፈው ዓርብ በጁፒተር ሆቴል በተደረገው ውይይት ከፓይለት ፕሮጀክቱ ጎን ለጎን በተመረጡ ቦታዎች ላይ በአዲስ መልክ ለሚከፈቱ ከ15 ዓመት በታች የእግር ኳስ ባለሙያዎች ማሠልጠኛ ጣቢያዎች መከፈት እንዳለባቸው ከባለድርሻ አካላቱ ጋር መግባባት ላይ መደረሱን ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ በማኅበራዊ ትስስር ገጹ ባሠራጨው መግለጫ ይፋ አድርጓል፡፡
እንደ መግለጫው ከሆነ በውይይቱ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ የስፖርት ኮሚሽን እንዲሁም ከትግራይ በስተቀር የዘጠኙ ክልሎችና የሁለቱ ከተማ አስተዳደር ስፖርት ኮሚሽነሮች፣ የትምህርት ቢሮ ተወካዮችና ፕሮጀክቱን በፋይናንስና መሰል ቁሳቁሶች ለመደገፍ ፈቃደኛ የሆነው የኢስት አፍሪካ ቦትሊንግ ካምፓኒ ተወካዮች መሳተፋቸውም ተነግሯል፡፡