በትግራይ ክልል በዕለት ደራሽ ምግቦች የፍትሐዊነት ችግሮች መስተዋላቸውን፣ የብሔራዊ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
በክልሉ የዕለት ደራሽ ምግቦች አቅርቦት ሥርዓቱን ጠብቆ እየሄደ ባለመሆኑ ምክንያት አቅርቦቱን ማግኘት ለሌለባቸው ሰዎች ማስተላለፍ፣ ድጋፉን ማግኘት ያለባቸው ሰዎች አለማግኘትና ከተሰጠው መመርያ ውጪ የቤተሰብ ቁጥርን መሠረት ሳያደርግ ዕርዳታ መስጠትና መሰል ዓይነት ችግሮች እንደሚስተዋሉ ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ ወ/ሮ እቴነሽ ንጉሤ ለሪፖርተር እንደተናሩት፣ በክልሉ ከሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦትና የድጋፍ ፈላጊዎች ቁጥር አለመጣጣም ጋር ተዳምሮ የአቅርቦቱ ፍትሐዊነት ላይ ተደጋጋሚ ችግር እየተነሳ ነው፡፡
የፌደራል መንግሥት በትግራይ ክልል የሕግ ማስከበር ዘመቻውን ከመጀመሩ በፊት፣ በክልሉ 1.8 ሚሊዮን ሰዎች በአስቸኳይ ጊዜ ዕርዳታ ይደረግላቸው እንደነበር ኮሚሽነሩ ገልጸዋል፡፡
ይሁን እንጂ ዘመቻው ከተጀመረበት ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. ወዲህ በተለያዩ ምክንያቶች ቁጥሩ መጨመሩን አካሄድኩት ባለው የመጀመርያ ጥናት፣ 700 ሺሕ ተጨማሪ ዜጎች መገኘታቸውን ኮሚሽነሩ ገልጿል፡፡
በአሁኑ ጊዜ ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል ተብለው ከተመዘገቡ ዜጎች ውስጥ ለሁለት ሚሊዮን ዜጎቸ፣ አራት ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ምግብ ማቅረብ መቻሉን አቶ ምትኩ ተናግረዋል፡፡
በክልሉ መንግሥትና በተለያዩ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች በትግራይ የአስቸኳይ ጊዜ ዕርዳታ የሚያስፈልጋቸው ሰዎች ቁጥር 4.5 ሚሊዮን ተብሎ የተያዘው፣ በክልሉ ሲከናወን ከነበረው የሕግ ማስከበር ዘመቻ ጋር ተያይዞ በባንኮች መዘጋት ምክንያት ነዋሪዎች ገንዘብ ማግኘት ባለመቻላቸውና በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች ተከስቶ በነበረው የበረሃ አንበጣ ምክንያት እንደነበር፣ አሁን ግን ነገሮች በመስተካከላቸው የተረጂዎች ቁጥር መቀነሱን አቶ ምትኩ አስረድተዋል፡፡
‹‹ይሁን እንጂ 4.5 ሚሊዮን የተባለውን ቁጥር ችግሩ በጣም አስከፊ ቢሆን በሚል አንደ መጨረሻ ነጥብ ይዘን ሥራ እየሠራን ነው፤›› ሲሉ ኮሚሽነር ምትኩ ገልጸዋል፡፡
የዕርዳታ አቅርቦቱን በ29 የትግራይ አካባቢዎች መድረሱ የተገለጸ ሲሆን፣ በቀሪዎቹና ባልተዳረሱት አካበቢዎች በተለይም አልፎ አልፎ ተኩስና መተማመን በማይቻልባቸው ቦታዎች በወታደር ታጅበው አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነ አቶ ምትኩ ተናግረዋል፡፡
በአንዳንድ አካባቢዎች የዕርዳታ አቅርቦት የጫኑ መኪኖች ወደ መጋዘንና ወይም ተረጂዎች መድረስ ሲገባቸው፣ ለሦስት ቀናት ያህል ሳይራገፉ ይታያሉ ብለዋል፡፡
ወደ ክልሉ የሚገቡ በተለይ ምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ ጭነቶች ያለምንም ችግር ወደ ትግራይ እንደሚገቡ አቶ ምትኩ አስታውቀዋል፡፡ ‹‹ነገር ግን በአንዳንድ አካባቢዎች በአንድ በኩል ዕርዳታ መጠየቅ፣ በሌላ በኩል ሳይራገፍ የሚቆይበት ሁኔታ ስላለ በቶሎ መፈታት አለበት፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞ የተወሰኑ የሕወሓት ሰዎች ባሉበት አካባቢ ጭነት የጫኑ መኪኖች እንዳይራገፉ ማስፈራሪያና ዛቻ እንዳለ፣ ይህንንም ችግር ለማስወገድ ከመከላከያ ሠራዊት ጋር በመሆን እየተሠራ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡