የማኅፀን ካንሰር ያክማል
የእናቶችና የሕፃናትን የሕክምና አገልግሎት እንግልት ለማስቀረት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሃያት አካባቢ ላይ 700 ሚሊዮን ብር ፈሰስ በማድረግ፣ በአበበች ጎበና ስም ዘመናዊ ሆስፒታል አስገንብቶ ወደ ሥራ ማስገባቱን አስታወቀ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ የሃይማኖት አባቶችና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች በተገኙበት የካቲት 4 ቀን 2013 ዓ.ም. ላይ ሆስፒታሉ ወደ ሥራ መግባቱ ተገልጿል፡፡
ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ እንደገለጹት፣ የአበበች ጎበና የእናቶችና የሕፃናት ሆስፒታል በወሊድ ወቅት እናቶች ላይ የሚደርሰውን የጤና ችግር ለመቀነስ ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡
ጤናማ ማኅበረሰብን ለመፍጠር እንደዚህ ዓይነት ዘመናዊ ሆስፒታሎችን በመገንባትና በማስፋፋት ማንኛዋም እናት በወሊድ ጊዜ እንዳትሞት ለማድረግ ዘመናዊ የሆነ አሠራሮችን ማጎልበት እንደሚያስፈልግም አስምረውበታል፡፡
ባለፉት 65 ዓመታት አገልግሎት ሲሰጥ የቆየውን ቀዳሚው የጋንዲ የእናቶችና የሕፃናት ሆስፒታልን በዘመናዊ መልኩ በማደስ ለአገልግሎት ምቹ ለማድረግ የሚሠራ መሆኑን ሳይጠቁሙ አላለፉም፡፡
በአሁኑ ወቅት ለአገልግሎት ክፍት የሆነውን ሆስፒታሉ በሚፈለገው ደረጃ ብቁና ጥራት ያለው አገልግሎት በመስጠት ለሌሎች የጤና ተቋሞች ምሳሌ መሆን እንዲችል የሚያስፈልገውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ምክትል ከንቲባዋ ተናግረዋል፡፡
400 አልጋዎች ያሉትና ዘመናዊ የጤና መረጃ አያያዝ ሥርዓትን የተከተለው አዲሱ ሆስፒታል ጥንቃቄ በተሞላ መልኩ በመያዝ ለትውልድ ትውልድ ማስተላለፍ ያስፈልጋል ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ዮሐንስ ጫላ (ዶ/ር) ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ሆስፒታሉ በእናቶች ላይ የሚደርሰውን የካንሰር በሽታና ተያያዥ ጉዳዮችን የሕክምና አገልግሎት በመስጠት ይሠራል፡፡ ሆስፒታሉ አዲስ እንደመሆኑ መጠን ወደፊት ሰፊ ሥራዎች የሚጠበቅበት ሲሆን፣ በእናቶች ላይ በሚከሰት ተጓዳኝ በሽታዎች የሕክምና አገልግሎት የሚሰጥ እንደሆነ ኃላፊው ገልጸዋል፡፡
በርካታ እናቶችና ሕፃናት በአገልግሎት ተደራሽነት ምክንያት በወሊድ ወቅት ለሞት መዳረጋቸውን ይሁን እንጂ በአሁኑ ወቅት ይህንን ችግር ለመፍታት የጤና ተቋሞችን በማስፋፋት ሰፊ ሥራ እየተሠራ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡
በአበበች ጎበና ስም የተሰየመው ሆስፒታል በአካባቢ ለሚኖሩ ነዋሪዎች ችግርን የሚያቃልል መሆኑን ኃላፊው አስረድተዋል፡፡
ሆስፒታሉም 400 አልጋ፣ 16 የምጥና የማዋለጃ ክፍሎች፣ ሰባት የቀዶ ጥገና ክፍሎች፣ ከ20 በላይ የተመላላሽ የሕክምና አገልግሎት መስጫ ክፍሎች ከእነ ሙሉ የሕክምና ቁሳቁሶች፣ የመረጃ አያያዝ ሥርዓቱ ከወረቀትና ከካርድ ነፃ በማድረግና ሌሎች ነገሮችን በማካተት ለአገልግሎት ክፍት እንዲሆን መደረጉ ተገልጿል፡፡