አጅቦት የነበረው የማረሚያ ቤት ፖሊስ መታሰሩ ተሰምቷል
ከሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ጋር በተያያዘ ለበርካታ ዓመታት ሲፈለግ ቆይቶ፣ ከሁለት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ በቁጥጥር ሥር ውሎ በእስር ላይ የነበረው ፍርደኛና ተከሳሽ እስረኛ፣ የካቲት 11 ቀን 2013 ዓ.ም. ከፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ቅጥር ግቢ ውስጥ ማምለጡ ታወቀ፡፡
ፍርደኛውና ተከሳሹ አቶ ኪዳኔ ዘካርያስ የሚባል ሲሆን፣ በሕገወጥ መንገድ ዜጎችን ወደ ተለያዩ አገሮች ‹‹እልካለሁ›› በማለት ከፍተኛ ገንዘብ በማስከፈል፣ ውቅያኖስ አቋርጠው ወደ ሌሎች አገሮች እንዲሻገሩ በማድረግ ሰጥመው ለመሞታቸው ምክንያት እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
ግለሰቡ ከ800 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች መሞት ምክንያት ከመሆኑም ባለፈ፣ የተለያዩ ሕገወጥ ድርጊቶችንም ያደርግ እንደነበር ተገልጿል፡፡ ከመሀል አገር ወደ ዓረብ አገሮች መሄድ የሚፈልጉ ንፁኃንን ገንዘብ በማስገደድና በማስገረፍ ጭምር ይነጥቅ እንደነበርም፣ የሪፖርተር ምንጮች ተናግረዋል፡፡
በዱባይ፣ በየመንና በተለያዩ አገሮች ይኖር ነበር የተባለው ግለሰብ፣ ኢትዮጵያ በኢንተርፖል በኩል ስታፈላልገው እንደነበርና በስዊዘርላንድና በጣሊያንም ይፈለግ እንደነበር ምንጮቹ ጠቁመዋል፡፡
በውጭ አገሮችም እንደሚፈለግ ያወቀው ግለሰቡ ራሱን ቀይሮ ኢትዮጵያ ውስጥ በመኖር ላይ እያለ፣ ከሁለት ዓመት በፊት ባስገረፈው ሰው ጠቋሚነት ተይዞና ተከሶ የተፈረደበት ቢሆንም፣ ሌላ ክስ ደግሞ ተመሥርቶበት ፍርድ ቤት በመመላለስ ላይ እያለ እንዳመለጠ ሪፖርተር ለማወቅ ችሏል፡፡
ግለሰቡ ሊያመልጥ የቻለው የካቲት 11 ቀን 2013 ዓ.ም. ለነበረው ቀጠሮ ወደ ልደታ ፍርድ ቤት ከአጃቢ ጋር ከሄደ በኋላ፣ መፀዳጃ ቤት ገብቶ በአጃቢ ፖሊስ እየተጠበቀ ባለበት ጊዜ ራሱ ይዞ ይግባ ወይም ሌላ ሰው ያስቀምጥለት ባይታወቅም፣ ልብሱን ቀይሮ ወጥቶ እንዳመለጠ ታውቋል፡፡ ግለሰቡን አጅቦ የነበረው የፌዴራል ማረሚያ ቤት ፖሊስ በዚህ ምክንያት ለጊዜው መታሰሩን የሪፖርተር ምንጮች ተናግረዋል፡፡ ግለሰቡ አደገኛ በመሆኑ የተቻለውን ሁሉ አድርጎ ከአገር ሊወጣ ስለሚችል፣ የፀጥታ ኃይሎች ከፍተኛ ክትትል እያደረጉ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡