. . . አሁንም አገር የሚያጠፋ ሃይማኖት የሚለውጥ ጠላት እግዚአብሔር የወሰነልንን ባሕር አልፎ መጥቷል . . . . በእግዚአብሔር ረዳትነት አገሬን አሳልፌ አልሰጠውም፡፡ . . . ያገሬ ሰው . . . ጉልበት ያለህ በጉልበትህ እርዳኝ፡፡ ጉልበት የሌለህ ለልጅህ፣ ለምሽትህ፣ ለሃይማኖትህ ስትል በኀዘን እርዳኝ፡፡ . . .ይህ ኃይለ ቃል ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ሕዝቡንና የየአካባቢውን መኳንንትና ገዢዎች በኢጣሊያ ላይ ያነሳሱበት የክተት አዋጅ ነበር፡፡ በዚህም አዋጅ መሠረትም ከ125 ዓመታት በፊት፣ የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም. ዓድዋ ላይ የኢጣሊያ ወራሪ ሠራዊት ድል ተመቶበታል፡፡ ኢትዮጵያውያን እርመኛ አርበኞች በጠቅላይ አዝማቹ በንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ ምኒልክ አማካይነት ሕያው ታሪክ ያስመዘገቡበት ዓድዋ፡፡
«ሃያ ሺሕ ያህል ወታደሮች ያሉበት የአውሮፓ ጦር በአፍሪካ ሰዎች ለመጀመሪያ ጊዜ ተሸነፈ፡፡ በእኔ እምነት መሠረት በዘመናችን ታሪክ ውስጥ እንደ ዓድዋው ያለ ጦርነት የለም፡፡ 25,000 ሰዎች በአንድ ቀን ጀንበር የሞቱበትና የቆሰሉበት ነው፡፡ ፖለቲካና ታሪክ አበቃ፡፡ ሀበሾች አደገኛ ሕዝቦች መሆናቸው ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ ተጽፎላቸዋል፡፡ የእኛ ዓለም ገና ቶር እና ኦዲዮን በሚባሉ አማልክት ሲያመልክ በነበረበት ጊዜ ሀበሾች ክርስትናን የተቀበሉ ናቸው፡፡» ይህንን የ19ኛው ምዕት ዓመት ታሪካዊ ገድል ነበር ጆርጅ በርክሌ በመጣጥፉ ያንፀባረቀውና “አጤ ምኒልክ” ከተሰኘው መጽሐፍ ላይ የሠፈረው፡፡
ከነገ በስቲያ፣ የካቲት 23 ቀን 2013 ዓ.ም. በመላው ኢትዮጵያ የዓድዋ ድል መታሰቢያ ይከበራል፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ መንግሥት መናገሻ ከተማ በአዲስ አበባ አራዳ ጊዮርጊስ በሚገኘው ዳግማዊ ምኒልክ ሐውልትና አደባባይ (በፎቶው ላይ የሚታየው የዓምናው አከባበር) እንደሁሌም በልዩ ሥነ ሥርዓት እንደሚከበር ይጠበቃል፡፡
የፎቶ መግለጫ
ከላይ የዓድዋው የኢትዮጵያና የኢጣሊያ ጦርነት በሠዓሊው ምናብ፣ (ከመሃል) በግራ ዳግማዊ ምኒልክ የኢጣሊያውን መሪ ክሪስፒን ሲጎሽሙትና ሲጥሉት በ‹‹ለ ፐቲት ጆርናል›› የታተመ የካርቱን ሥዕል፣ አዝማሪ ፃዲቄ እየሸለለችና እየፎከረች ስታዋጋ በሠዓሊው ምናብ፣ (ከታች) በግራ ደጃዝማች ባልቻ፣ ራስ አሉላ፣ ዳግማዊ ምኒልክ፣ እቴጌ ጣይቱ፣ ራስ መንገሻ፣ ራስ መኰንን እና ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ