ከስምንት ወር በፊት ለቶኪዮ ኦሊምፒክ ዝግጅት የጀመረው የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ለሁለተኛው ምዕራፍ ዝግጅት ከአዲስ አበባ ውጪ በሆኑ ቦታዎች እንዲሆን መወሰኑን አስታወቀ፡፡ ከሰሞኑ ከኦሊምፒክ ኮሚቴና ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን፣ እንዲሁም የየውድድር ዓይነቱ ዋና አሠልጣኞች፣ ከአትሌቶችና ከሐኪሞች የተውጣጣ ኮሚቴ ተዋቅሮ ለምዕራፍ ሁለት ዝግጅት ምቹ የሆኑ ቦታዎችን ቅኝት አድርጓል፡፡
ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴው በማኅበራዊ ትስስር ገጹ እንዳስታወቀው፣ የቦታ ቅኝት ያደረገው ኮሚቴ ከየካቲት 19 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ በሐዋሳ ከተማና አካባቢው እንዲሁም በሻሸመኔ ዙሪያ የሚገኙ ለልምምድ ምቹ የሆኑ ቦታዎችን ተመልክቷል፡፡ የቅኝት ኮሚቴ አባል ከሆኑት አትሌቶች መካከል ለሁለት ተከታታይ ጊዜ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮኑ ሙክታር እድሪስና ብቸኛዋ የእርምጃ ተወዳዳሪ የኋልዬ በለጠው መካተታቸው ተጠቁሟል፡፡
ታላቁ አትሌት ኃይሌ ገብረ ሥላሴን ጨምሮ ሌሎችም የዘርፉ ሙያተኞች አዲስ አበባና አካባቢዋ አሁን ላይ ያለው የአየር ፀባይ በተሽከርካሪዎችና ፋብሪካዎች ጢስ የተበከለ በመሆኑ፣ በዚች ከተማ ስፖርተኞችን በሆቴል አስቀምጦ ዝግጅት ማድረግ ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ሲናገሩ እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ሁለቱ አካላት ይህንኑ ከግምት በማስገባት ለብሔራዊ ቡድኑ የሚመጥን የዝግጅት ሥፍራ ከአዲስ አበባ ውጪ መምረጣቸው ተገቢና ትክክለኛ ውሳኔ መሆኑም እየተነገረ ይገኛል፡፡ በዚሁ ጉዳይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ሙያተኞች ሐዋሳ ከተማ ለትራክ ውድድር ዝግጅት አልቲትዩዱ ዝቅ ያሉና ለፍጥነት ሥራ ምቹ ቢሆንም፣ ነገር ግን ደግሞ የሒዩሚዲቲው (ወበቁ) መጠን በተቃራኒው የአትሌቶች ውጤት ላይ ተፅዕኖ ሊኖረው እንደሚችል ይሠጋሉ፡፡ ሙያተኞቹ ለዚህ መፍትሔ የሚሉት ደግሞ አትሌቶቹን በሀገረ ሰላም በማስቀመጥ ለትራክ ልምምድ ቀን ብቻ ወደ ሐዋሳ ሄደው ልምምድ እንዲያደርጉ ማመቻቸት እንደሚገባ ሙያዊ ምክራቸውን ከመስጠት አልተቆጠቡም፡፡