በምሕንድስናው፣ በኢኮኖሚው፣ በአካዴሚውና በሌሎችም መስኮች የተሰማሩ ኢትዮጵያውያን ተሰባስበው ‹‹ኢትዮጵያ 2050›› የተሰኘ ዓለም አቀፍ ጉባዔ በወርኃ ጥር በአዲስ አበባ አካሂደው ነበር፡፡ የጉባዔው ዓላማ ኢትዮጵያ ከ30 ዓመታት በኋላ ሊገጥሟት በሚችሉ ጉዳዮች ላይ በማተኮር ሊያጋጥሙ በሚችሉ ችግሮችና ሥጋቶች ላይ ያጠነጠነ ነበር፡፡ ከጉባዔተኞቹ መካከል በኩር መሐንዲስ ታደሰ ኃይለ ሥላሴ (ኢንጂነር) ይገኙበታል፡፡
እሳቸው በተለያዩ ጊዜያት ያቀርቧቸው በነበሩት የልማት አስተያየቶች ላይ በመመርኮዝ ነበር የመሐንዲሶች የጥናት ቡድን በ2011 ዓ.ም. ተመሥርቶ በ2050 ኢትዮጵያ በልማት የት ልትደርስ ትችላለች የሚለው መድረክ የተዘጋጀው፡፡
በኩር መሐንዲስ ታደሰ ኃይለ ሥላሴ (ኢንጂነር)፣ አቅርበውት የነበረው ሐሳብ በደጋማው አካባቢ ያለውን ውኃ ወደ ቆላማው አካባቢ መውሰድ ስለሚቻልበት ሳንሳይዊ ዘዴ ያስረዳ ነበር፡፡ ቆላማ አካባቢ ሰፊ መሬት አለ፣ ውኃ ግን የለም፡፡ ደጋማው አካባቢ ደግሞ ውኃው አለ፣ መሬቱ ግን የለም፡፡ ይህንን ለማጣጣም ትልልቅ ወንዞች የሚገኙባቸው የደጋማ አካባቢዎችን ለቆላማ አካባቢዎች መጋቢ ማድረግ ይቻላል የሚል ሐሳብ ነበር፡፡
‹‹ሰሜን ሸዋ ውስጥ ያሉትን ትልልቅ ወንዞች እንጦጦን በመቁረጥ፣ በአዲስ አባባ በኩል ወደ አዋሽ ወንዝ እንዲፈሱ ማድረግ የሚቻልበት ዕድል አለ፡፡ አሚባራ ላይ እንደተፈጠረው ሁሉ እነዚህን ወንዞች በመጠቀም ትልቅ የመስኖ እርሻ ሥራ ማስፋፋት የሚቻልበት ዘዴ አለ፡፡ በወንጂና በመተሐራ የተፈጠረውን ትልቅ የመስኖ ሥራ በዚህ ሐሳብ መሠረት መፍጠር ይቻላል፡፡ እንዲህ ያሉ ትልልቅ ሐሳቦች ወጣ ያለ አሠራር እንድንከተል ይጋብዙናል፡፡
ከተማችን አሁን በያዝነው ልማዳዊ መንገድ መደረጃት የለባትም፡፡ የከተማ ሥልጣኔ፣ የከተማውን ሕዝብ ቁጥር ያገናዘበ፣ የመንገድ፣ የውኃ፣ የመብራት፣ የቤትና የሌሎችንም አቅርቦቶች ያቀናጀ አካሄድ መፍጠር የሚያስችል ሐሳብ ካላመጣን በቀር፣ አገራችን ትልቅ ፈተና ውስጥ ትገባለች፡፡ ፈተናው ደግሞ ከባድና ኃይለኛ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ዕድሎች አሉን ሲሉ ነበር ዓምና በዓለም አቀፉ ጉባዔ ያንፀባረቁት፡፡
በኩር መሐንዲሱ በምሕንድስና ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ከተመረቁ በኋላ፣ ልምድ ለማግኘት በቀን ሙያተኛነት በመቀጠር፤ አሁን ጠቅላይ ፖስታ ቤት ያለበት ሕንፃ በሚገነባበት ጊዜ አገልግሎት ከማበርከታቸውም ባለፈ በዚህ ፕሮጀክት ላይ እየታዩ ደረጃ በደረጃ እስከ ፕሮጀክቱ ዋና መሐንዲስነት ድረስ ማገልገላቸው ገጸ ታሪካቸው ያሳያል፡፡
በመቀጠልም ‹‹ታደሰ ኃይለ ሥላሴ ኮንስትራክሽን›› በሚል የራሳቸውን ከማቋቋም ባሻገር ድርጅቱን በማሳደግና ከኢንጂነር ብርሃነ አባተ ጋር በመሆን ‹‹በርታ ኮንስትራክሽን›› የተሰኘ አገር በቀል ተቋም አቋቋመዋል፡፡
ከቀደምቱ አገር በቀል ተቋራጮች አንዱ የሆነው የነኢንጂነር ታደሰ በርታ ኮንስትራክሽን፣ ከተሳተፈባቸው የተለያዩ የመንገድ ሥራዎች ውስጥ ብቸና ሞጣ፣ ጅማ ጭዳ፣ ሰርዶ አፍዴራ፣ ጋሸና ላሊበላ፣ እንዲሁም በፋብሪካ ግንባታም የሐረር ቢራ ፋብሪካና ሜታ ቢራ ፋብሪካ ሲገኝበት፣ ለቱሪስት መዳረሻ የሚሆኑ ታሪካዊ ቦታዎች ውስጥ በባህር ዳር ‹‹ጣና ሐይቅ››፣ በጎንደር ‹‹ጎሐ›› በላሊበላ ‹‹ሮሃ››፣ በአክሱም ‹‹ይሓ›› አራት ሆቴሎችን መገንባቱ ተመዝግቧል፡፡ በኩር መሐንዲስ ታደሰ በገጸ ታሪካቸው እንደተመለከተው፣ በሰፋፊ የመስኖ ሥራ ተግባራትም እንደ የአሚባራ መስኖ ፕሮጀክት የመሰለ ተሳትፈዋል፡፡
ከአባታቸው ከአቶ ኃይለ ሥላሴ ተክለ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ እልፍነሽ ወልደመድኅን በቀድሞው አርሲ ጠቅላይ ግዛት ዶዶታ ወረዳ ሊጋባ ከተማ፣ ጥቅምት 14 ቀን 1933 ዓ.ም. የተወለዱት ኢንጂነር ታደሰ ኃይለ ሥላሴ፣ በሰባት ዓመታቸው ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በተፈሪ መኰንን ትምህርት ቤት እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡
በመቀጠል በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ በ1953 ዓ.ም. የምሕድስና ኮሌጅ በመግባት በ1957 ዓ.ም. ትምህርታቸውን አጠናቅቀው ተመርቀዋል፡፡ በትምህርት ቤት በነበሩበት ጊዜ ጀምሮ በነበራቸው የአገር ፍቅር የተነሳ በወቅቱ በነበረው ‹‹ተምሮ ማስተማር›› በሚባል ፕሮግራም ተሳታፊ እንደነበሩ ገጸ ታሪካቸው ያስረዳል፡፡
ኢንጂነር ታደሰ ኃይለ ሥላሴ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ80 ዓመታቸው የካቲት 22 ቀን 2013 ዓ.ም. ሥርዓተ ቀብራቸው በማግስቱ በአራዳ በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡
በሚያዝያ 1967 ዓ.ም. ከወ/ሮ ሒሩት አማረ ጋር ትዳር መሥርተው እስከ ዕለተሞታቸው ድረስ ለ46 ዓመታት አብረው የኖሩት የበኩሩ መሐንዲስ ታደሰ ኃይለ ሥላሴ ዜና ዕረፍት ተከትሎ የኢትዮጵያ ሲቪል መሐንዲሶች ማኅበር ባወጣው የሐዘን መግለጫ፡ ከ1990 ዓ.ም. ጀምሮ ማኅበሩን በመመሥረትና ከመደበኛ አባልነት እስከ የሥራ አስፈፃሚ ቦርድ ከመሆን ባለፈ በዕውቀትና በገንዘብ ሲደግፉ የቆዩ መሆናቸውን አመልክቷል፡፡
‹‹ስለ አገር ልማት የነበራቸው ህልም ከፍ ያለ ነበር፡፡ በተለያዩ መድረኮች ለአገር ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያደርጉ የሚችሉ ሐሳቦችን አቅርበዋል፡፡ ያገባኛል የሚሉ ወገኖችም በሐሳባቸው ዙሪያ እንዲወያዩ አድርገዋል፡፡ በተጨማሪ ኢንጂነር ታደሰ ኃይለ ሥላሴ ስለ አገር ልማት ጽሑፎችን ለሕዝብ በተደጋጋሚ አበርክተዋል፡፡ እንዲሁም በዚሁ ጥረት በሕዝብ ሚዲያዎች ብዙ ገለጻዎችን አከናውነዋል፤›› ሲልም አወድሷቸዋል፡፡