‹‹የሰው ልጅ በሕይወት ዘመኑ በተለያዩ መንገዶች ያልፋል፡፡ ሁሉም ሰው የሚያልፍበት የሕይወት ጎዳና፣ ፈተናውና ስኬቱም የአንዱ ከሌላኛው ይለያል፡፡ ሰዎች ኑሮ ከበደኝ፣ እያለፍኩበት ያለው ፈተና ከአቅሜ በላይ ነው የሚል የተስፋ መቁረጥ ስሜት የሚሰማቸው ከሆነ፣ ይህን የመከላከያው አንዱ መንገድ የሌሎችን የሕይወት ውጣ ውረድ መስማትና ማንበብ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህን ችግር አላልፈውም፣ ከዚህ በላይ መቋቋም የምችለው መከራ የለም፣ በቃኝ! ለምንል ሰዎች፣ የተለያየ የሕይወት ተሞክሮ ያላቸው ሰዎች፣ ያለፉበትን የኑሮ ውጣ ውረድና ድል ስንሰማ፣ ስናነብና ስንመለከት፣ የሕይወት ስንቅና ብርታት ይሆነናል፡፡››
ይህን ኃይለ ሐረግ በመጽሐፉ ያሰፈረው አንተነህ ድፋባቸው ‹‹ስደተኛው ሼፍ›› በሚል ርዕስ በደረሰው ግለታሪኩ ላይ ነው፡፡
‹‹ብዙ ጊዜ በተለይ በልጅነትና በወጣትነት ያሳለፍኩትን የሕይወት ውጣ ውረድ፣ መውደቅና መነሳት፣ ተስፋ ማጣትና ተስፋ ማድረግ ለመጻፍ ጉጉት ነበረኝ፤ ያለው ደራሲው፣ ግለ-ሕይወት ታሪኩን ለመጻፍ ያነሳሳው፣ ልጅነቱንና ወጣትነቱን አጠናቅቆ ወደ ጉልምስና እየተጠጋ ባለበት ዕድሜው ላይ ለመድረስ ያሳለፈውን ውጣ ውረድ፣ ለብዙ ወጣቶች የተሞክሮ ምሳሌና መማሪያ ይሆናል ብሎ በማሰብ ነው ሲል አክሏል፡፡
ከሁለት አሠርታት በፊት በግለሰቦች ማንነት ላይ የተመሠረቱ የሕይወት ታሪክ ወይም ግለ-ሕይወት ታሪክ መጻሕፍት ቁጥር በእጅ ጣት የሚቆጠሩ እንደነበሩ ያስታወሱት በመጽሐፉ ላይ አስተያየት የሰጡት ደራሲው አቶ ብርሃኑ ሰሙ፣ አሁን ላይ ይህ ዘርፍ ራሱን የቻለ አንድ የመጻሕፍት መለያ ሆኖ በመታወቅ ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡
በሆቴል ዘርፍ ካለ ሙያዎች አንዱ በሆነው በ‹‹ሼፍ›› ሙያ ላይ የተሰማራው አቶ አንተነህ ድፋባቸው፣ በብዙ የኑሮ ከፍታና ዝቅታዎች ውስጥ አልፎ፣ ከአገሩ ባለፈ በጀርመን በሚገኝ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴል በሙያው ማገልገል ላይ እንደሚገኝም አውስተዋል፡፡
በ120 ብር የተተመነው መጽሐፉ ባለ 215 ገጾች ሲሆን፣ ከደራሲው ዓውደ ሕይወት ጋር የተያያዙ አሥር ባለቀለም ፎቶዎችን አካቷል፡፡